Quantcast
Channel: Federal Supreme Court Cassation Bench
Viewing all 116 articles
Browse latest View live

የሰበር ችሎት የህግ ቃላት መፍቻ

$
0
0

የሰበር ችሎት የህግ ቃላት መፍቻ

የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የሚሰጠው የህግ ትርጉም በየትኛውም ደረጃ ላይ በሚገኙ የክልል እና የፌደራል ፍ/ቤቶች የአስገዳጅነት ውጤት እንዲኖረው የፌደራል ፍርድ ቤቶች አዋጅን እንደገና ለማሻሻል በወጣው አዋጅ ቁ. 454/1997 ከተደነገገበት ጊዜ ጀምሮ ባሉት አስር ዓመታት ውስጥ ችሎቱ ካከናወናቸው አመርቂ ስራዎች መካከል ለህግ ቃላት ፍቺ ማበጀት አንዱና ዋነኛው ተደርጎ ሊጠቀስ ይችላል፡፡ ፈታኝ በሆነው ህግን የመተርጎም ስራ ውስጥ የቃላትንና ሐረጋትን ትክክለኛ ይዘት መወሰን እና የህግ ዕውቀት የሌለው ሰው በሚገባው ቀላልና አጭር አገላለጽ ትርጓሜያቸውን ማስቀመጥ ትልቁን ቦታ ይይዛል፡፡

አንዳንድ ቃላት ከህግ ጋር በተያያዘ ካልሆነ በቀር በዕለት ተዕለት የማህበረሰቡ የቋንቋ አጠቃቀም ግልጋሎት የላቸውም፡፡ ለምሳሌ ህግ ጠቀስ ባልሆነ ንግግር “እከሊት/ሌ እኮ ዳረገኝ/ችኝ” አንልም፡፡ መዳረግ፣ ዳረጎት ትርጉም የሚኖረው በህግ ግንኙነት ውስጥ ብቻ ነው፡፡ ለእነዚህና መሰል ቃላት በቀላሉ የሚገባ ፍቺ ካልተበጀ በስተቀር ህግ አዋቂውና የህግ ዕውቀት በሌለው የህብረተሰብ ክፍል መካከል መግባባት፣ መደማመጥ አይኖርም፡፡ አንዳንዴ በህግ ሙያተኛው ዘንድ ራሱ የህግ ቋንቋ የባቢሎን የሚሆንበት አጋጣሚ ይፈጠራል፡፡ አንዳንድ ቃላት በህግ አውጪው ሆነ ተርጓሚው ቁርጥ ያለ ትርጓሜ ስለማይሰጣቸው በአጠቃቀም ረገድ ልዩነት ይከሰታል፡፡ ለምሳሌ ከህግ ውጭ፣ ህገ-ወጥ፣ ህግ መጣስ፣ ህግ መተላለፍ፣ ህጋዊ ያልሆነ፣ የህግ መሰረት የሌለው የሚሉ ቃላትና ሐረጋት ጥቅም ላይ የሚውሉበት ሁኔታ ወጥነት አይታይበትም፡፡

ወጥነትን በማስፈን ረገድ ትልቁን ሚና መጫወት ያለባቸው ፍርድ ቤቶች ናቸው፡፡ የፍ/ቤቶች የህግ ቃላት ፍቺ በሌላው ዓለም ዘንድ በህግ መዝገበ ቃላት ዝግጅት ውስጥ ከሚያበረክቱት አስተዋጽኦ በተጨማሪ ብቻቸውን የዳኝነት መዝገበ ቃላት (Judicial Dictionary) ሆነው ይጠናቀራሉ፡፡ በዚህ ረገድ Stroud’s Judicial Dictionary እና West Publishing Company ያዘጋጀው Judicial and Statutory Definitions of Words and Phrases ተጠቃሽ ናቸው፡፡ የሰበር ችሎት የህግ ቃላት ፍቺዎች ወደፊት የአማርኛ የህግ መዝገበ ቃላት ቢዘጋጅ በዋነኛ ምንጭነት በማገልገል ትልቅ ፋይዳ ይኖራቸዋል፡፡

በግሌ ከለቀምኳቸው ከቅፅ 1 እስከ 19 ድረስ በታተሙት የሰበር ውሳኔዎች (በከፊልም ባልታተሙት) ውስጥ የሚገኙ የህግ ቃላት ፍቺዎች መካከል የከፊሎቹ በዝርዝር ከዚህ በታች ቀርቧል፡፡ ሁሉም ቃላት በመደበኛ መዝገበ ቃላት እንደምናገኘው ዓይነት ትርጓሜ አልያዙም፡፡ ስለሆነም ከአገባብ በመነሳት ለፍቺ እንዲያመቹ ተደርገው ተሰካክተዋል፡፡ የተወሰኑ ቃላት ደግሞ ህግ አውጭው ትርጓሜያቸውን የወሰናቸው ሆኖም ግን በችሎቱ ተጨማሪ ማብራሪያ የዳበሩ ናቸው፡፡

ሀብትሽ በሀብቴ

ባልና ሚስት ከጋብቻ በፊት ያፈሩትን የግል ንብረት የጋራ ለማድረግ የሚስማሙበት የጋብቻ ውል

“ሀብትሽ ሀብቴ ነው” የሚለው የአማርኛ ሐረግ የሚታወቀው ተጋቢዎች በግል የነበራቸውን ሀብት የጋራ ለማድረግ በማሰብ የሚጠቀሙበት ስለመሆኑ ከነባራዊ ሁኔታ የምንረዳው ጉዳይ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 98029 ቅጽ 18፣[1] ፍ/ህ/ቁ. 1732፣ 1734-1738

መሠረታዊ የህግ ስህተት

ስህተቱ ሳይታረም በመቅረቱ ምክንያት ውጤቱ ሊለወጥ ያልቻለ ወይም በተከራካሪው ወገን ፍትህ የማግኘት መብት ላይ መሠረታዊ ለውጥ የሚያመጣ

ሰ/መ/ቁ. 86187 ቅጽ 15፣[2] ኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ህገ መንግስት አንቀጽ 80(3) ሀ፣ የፌደራል ፍርድ ቤቶች አዋጅ ቁ. 25/1998 አንቀጽ 10፣ 22፣ ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 207

መስቀለኛ ይግባኝ

በይግባኝ ክርክር መልስ ሰጪ የሆነው ወገን በቀጥታ ይግባኝ ሳያቀርብ ተገቢውን ዳኝነት ከፍሎ ይግባኝ ባዩ ባቀረበው
የይግባኝ ክርክር በመልስ ሰጪነት ከሚያቀርበው ክርክር ጋር በፍርዱ ቅር በመሰኘት የሚያቀርበው ይግባኝ

መስቀለኛ ይግባኝ ስለሚስተናገድበት ስርዓት በሕጉ በተለየ ሁኔታ በግልጽ የተመለከተ ነገር እስከሌለ ድረስ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ. 337 እና 338 ድንጋጌዎች የተመለከተው የክርክር አመራር ስርዓት ለመስቀለኛ ይግባኝም በተመሳሳይ ሁኔታ ተፈጻሚነት የሚኖረው በመሆኑ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ. 340(2) በተመለከተው መሰረት መልስ ሰጪው ወገን የሚያቀርበው የይግባኝ ማመልከቻ ግልባጭ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ.ቁ. 338 መሰረት ለይግባኝ ባዩ እንዲደርስ ሊደረግ የሚችለው ይግባኙ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/.ቁ. 337 መሰረት ያልተሰረዘ በሆነ ጊዜ ብቻ ነው፡፡ በመሆኑም መልስ ሰጪው ወገን ያቀረበው የይግባኝ አቤቱታ ከተሰማ በኋላ የሌላኛውን ወገን ክርክር መስማት ሳያስፈልግ ይግባኙ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ. 337 መሰረት እንዲሰረዝ የሚሰጥ ትዕዛዝ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ. 340(2) የተመለከተውን የክርክር አመራር ስርዓት የሚቃረን ነው ለማለት አይቻልም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 92043 ቅጽ 16፣[3] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 337፣ 338፣ 340/2/

መቀበር መብት(የ—)

በአንድ ወቅት የአንድ ሃይማኖት ተከታይ የነበረ ሰው ከሃይማኖት ተቋሙ በተሰጠው ልዩ ፈቃድ
ለስርዓተ ቀብሩ መፈጸሚያ እንዲሆነው በቅጥር ግቢ ውስጥ የመቃብር ቤት አሰርቶ ከመሞቱ በፊት
ሃይማኖቱን ቢቀይር ባሰራው መቃብር ቤት “የመቀበር መብት” አይኖረውም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 85979 ቅጽ 15፣[4] ፍ/ህ/ቁ. 1179፣ ኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ህገ መንግስት አንቀጽ 13፣ 27/1/፣ ዓለም ዓቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ሁለተናዊ መግለጫ አንቀጽ 18፣ ዓለም አቀፍ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ቃል ኪዳን ስምምነት አንቀጽ 18(1)

መብት መርጋት(የ—)

የመብት መፅናት፣ በህግ ዕውቅና ማግኘትና መረጋገጥ

የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1168/1/ የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለእጅ /ባለይዞታ/ የሆነ ሰው የዚሁኑ ንብረት ግብር ባለማቋረጥ 15 ዓመት በሥሙ ከከፈለ የዚሁ ሀብት ባለቤት ይሆናል በሚል ደንግጐ ይገኛል፡፡ ሕጉ ይርጋ አዘል ስለሆነ የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለእጅ /ባለይዞታ/ የሆነው ሰው የዚህን ንብረት ግብር ባለማቋረጥ ለ15 ዓመት በሥሙ ከከፈለ ሌላ ይገባኛል የሚል ሰው እንዲሰጠው ሊጠይቀው አይችልም፡፡ በሕጉ ለባለይዞታው መብቱ ይረጋለታል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 15631 ቅጽ 3፣[5] ፍ/ህ/ቁ. 1168(1)

መከላከያ ማስፈቀጃ (የ-)

በአጭር ስነ ስርዓት ታይቶ እንዲወሰን ክስ በሚቀርብበት ጊዜ ተከሳሹ ክሱን ለመከላከል እንዲፈቀድለት የሚያቀርበው አቤቱታ

በአጭር ሥነ ሥርዓት እንዲታይ በሚቀርብ ክስ አመራር ሥርዓት ተከሳሽ ለመከላከል እንዲፈቀድለት ያቀረበው ጥያቄ ተቀባይነት በፍ/ቤቱ አግኝቶ የተጠየቀውን ገንዘብ ላለመክፈል በቂ ምክንያት መሆን አለመሆኑ የሚታወቀው ፍ/ቤቱ ከአጭር ሥነ ሥርዓት ወደ መደበኛ የክርክር ሥነ ሥርዓት ውስጥ በመግባት ግራ ቀኙን በአግባቡ በማስረጃ ካከራከረ በኋላ ነው፡፡

የፈቃድ ጥያቄ ደረጃ ላይ የቼክ ባሕርይ ሳይሆን መታየት ያለበት ተከሳሽ ለመከላከል እንዲፈቀድለት ያቀረበው ምክንያት ፈቃድ የሚያሰጥ መሆን አለመሆኑን ነው፡፡ የፍሬ ነገር ክርክር ከፈቃድ በኋላ የሚታይ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 43315 ያልታተመ፣[6] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 284-286

መድን ጥቅም(የ—)

የመድን ጥቅም /insurable interest/ ያለው ሰው ሲባል በደረሰው አደጋ ወይም ጉዳት በትክክል የተጎዳ ወይም ሊጎዳ የሚችል ሰው ማለት ነው፡፡

መድን ሰጪው ካሣ የሚቀበለው ጉዳት በደረሰበት ወቅት ጉዳት በደረሰበት ንብረት ወይም እቃ ላይ የመድን ጥቅም ያለው ሰው ሲሆን የመድን ጥቅም የሌለው ሰው ካሣ ለመጠየቅ የሚያስችለው የሕግ መሰረት የለውም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 47004 ቅጽ 13[7]

ረቂቅ ውል

የተዋዋይ ወገኖች ፊርማ ያላረፈበት ወይም ስምምነታቸው ተሞልቶ ያልተጻፈበት ውል

በፍታብሔር ሕግ ቁጥር 1720 ንኡስ አንቀጽ 1 ድንጋጌ መሰረት አንድን ውል እንደረቂቅ የሚያስቆጥረው የውሉ በሚገባ አኳኋን በፍታብሔር ሕግ ቁጥር 1726 መሰረት የተስማሙበትን ሞልተው አለመፃፋቸው፣ በፍታብሔር ሕግ ቁጥር 1727/1/ መሰረት ተዋዋዮች ያልፈረሙበት ሲሆንና በፍታብሔር ሕግ ቁጥር 1728 ንኡስ አንቀጽ 1 እና ንኡስ አንቀጽ 2 መሰረት ተዋዋዮቹ ፊርማቸውን ያላስቀመጡ ሲሆን ነው፡፡ ከዚህ ውጭ ውሉ የተዋዋዮቹን ስምምነት በሚገልጽ መንገድ በጽሐፍ ተዘጋጅቶ ተዋዋዮቹ ከፈረሙበት በኋላ ምስክሮች ሣይፈርሙበት ቢቀሩ የውሉን ሰነድ እንደረቂቅ የሚያስቆጥር ጉድለት እንዳልሆነ ከፍታብሔር ሕግ ቁጥር 1727 ንኡስ አንቀጽ 2 ድንጋጌ ለመረዳት ይቻላል፡፡ በተዋዋዮቹ የተፈረመው ውል ላይ ምስክሮች ሣይፈራረሙ ቢቀሩ ውሉ እንደረቂቅ የሚታይ ሣይሆን ውሉን ውጤት አልባ የሚያደርግ ጉድለት ስለመሆኑ ከፍታብሔር ሕግ ቁጥር 1727/2/ ድንጋጌ ለመረዳት ይቻላል፡፡ በሌላ በኩል በልዩ ሁኔታ የቤት ሽያጭ ውል በጽሑፍ ሳይይደረግ ቢቀር እንኳን እንደረቂቅ የሚታይ ሣይሆን ውሉ ፈራሽ እንደሚሆን ከፍታብሔር ሕግ ቁጥር 2877 ድንጋጌ ለመረዳት ይቻላል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 34803 ቅጽ 8[8]

(የአንድ ዳኛ የልዩነት ሀሳብ)

ባልና ሚስትነት ሁኔታ(የ—)

ሁለት ሰዎች የባልና ሚስትነት ሁኔታ አላቸው የሚባለው ባልና ሚስት ነን እየተባባሉ አብረው
የሚኖሩ እንደሆነና ቤተዘመዶቻቸውና ሌሎች ሰዎች በዚሁ ሁኔታ መኖራቸውን ሲያረጋግጡላቸው ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 21740 ቅጽ 5፣[9] ፍ/ህ/ቁ. 699፣ 708

ተከሳሽ ከሳሽነት ክስ(የ—)

ተከሳሽ የሆነ ወገን በተከሰሰበት መዝገብ ላይ በተራው በከሳሹ ላይ የሚያቀርበው ክስ

ንብረት ለማስመለስ በቀረበ ክስ ላይ ንብረቱ የሚመለስ ከሆነ ተከሳሽ በንብረቱ ላይ ያፈሰሰውን ሀብት /ያወጣውን ወጪ/ መጠየቅ የሚችለው በተከሰሰበት መዝገብ ተገቢውን ዳኝነት ከፍሎ የተከሳሽ ከሳሽነት ክስ /ወይም ሌላ አዲስ ክስ/ በማቅረብ እንጂ በመከላከያ መልሱ ላይ በሚያቀርበው መከራከሪያ አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 86454 ቅጽ 15[10] ፣ ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 234(1) ረ፣ 215(2)

አመዛኝ ግዴታ

የውል አብዛኛው ወይም መሰረታዊ ግዴታ፣ ዓይነተኛ ግዴታ

ዓይነተኛ የሆነ ወይም መሰረታዊ የውል ግዴታ መጣስ ከሌለ በቀር ተዋዋይ ወገኖች ጥቃቅን ምክንያቶችን ብቻ በመስጠት ውሉ እንዲፈርስ ማድረግ አይችሉም፡፡ የቤት ሽያጭ ውል አመዛኙ ግዴታ በተፈጸመ ጊዜ የተወሰነ ቀሪ ገንዘብ አለመከፈሉ ውሉን ለማፍረስ የሚያበቃ መሠረታዊ የግዴታ መጣስ አልተፈጸመም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 18768 ቅጽ 4፣[11] ሰ/መ/ቁ. 57280 ቅጽ 13፣[12] ፍ/ህ/ቁ. 1771(1)፣ 1785(2)፣ 1789

አር.ቲ.ዲ. (RTD)

የተፋጠነ የወንጀል ክርክር ስርዓት

የጉዳዮችን መራዘም ለማስቀረት የተቀየሰው የተፋጠነ የወንጀል አሰጣጥ (RTD) መሰረታዊ ዓላማ በማስረጃ ደረጃ ውስብስብነት የሌላቸውን ጉዳዮች በቀላሉ ለመወሰን አዲስ አሠራር ለመዘርጋት ማስቻል ከሚሆን በስተቀር በሕገ መንግስቱና በሌሎች ተፈጻሚነት ባላቸው ሕጎች የተጠበቁትን የተከሳሽን መብቶች በሚጎዳ አኳኃን ለመተግበር አለመሆኑ ይታወቃል፡፡ በመሆኑም በሕጉ የተጠበቁት መብቶችና የዳኝነት አካሄዶች በሕጉ አግባብ ተተግብረው ዳኝነት ከሚሰጥ በስተቀር አንድ ጉዳይ የተፋጠነ የወንጀል አሰጣጥን (RTD) መሰረት አድርጎ በመቅረቡ ብቻ ቀሪ የሚሆኑ አይደሉም፡፡ የተፋጠነ የወንጀል አሰጣጥ (RTD) አሰራርን መሰረት አድርጎ የሚታይ ጉዳይ የተከሳሹን የመከላከል መብት ለመተው የሚያስችለው ተከሳሹን ይህንኑ መብቱን በማሻያማ አኳኃን የተወው መሆኑን ሲያረጋገጥ ነው፡፡

የተከሳሽ ክስን የመከላከል መብት ሊታለፍ የሚገባው ተከሳሹ መብቱን የማይጠቀምበት መሆኑን በግልፅ ለፍርድ ቤቱ ሲያረጋግጥለት ብቻ ነው፡፡ ተከሳሹ መብቱን ስለመተዉ ባልተረጋገጠበት አግባብ ግን የተከሳሽን የመከላከል መብት ተከሳሹ ትቷል የሚል አገላለፅ በፍርድ ሐተታው ላይ በማስፈር ብቻ ዳኝነት መስጠት ተገቢነት የሌለው አካሄድ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ 100712 ቅጽ 17፣[13] ኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ህገ መንግስት አንቀጽ 9/4/፣ 13/1/ እና /2/፣ 20/4/

አቤቱታ ፅሁፍ(የ—)

ከሳሽ የሚጠይቀውን ሁሉ ዘርዝሮ የሚገልፅ ፅሁፍ፣ ተከሳሽ የሚሰጠው የመከላከያ ፅሁፍ፣
የተከሳሽ ከሳሽ የሚያቀርበው ፅሁፍ፣ የይግባኝ ማቅረቢያ ፅሑፍ ወይም በሌላ አይነት
ተፅፎ ለፍርድ ቤትና ክስ መነሻ ወይም ለዚሁ መልስ የሚመለከት ማናቸውም ፅሑፍ

የባልና ሚስትነት የምስክር ወረቀት ለማግኘት የሚቀርብ አቤቱታ፣ ባል ወይም ሚስት ነኝ በማለት አንድ ሰው የሚያቀርበውን ማመልከቻና መግለጫ ብቻ የሚመለከት አይደለም፡፡ የባልና ሚስትነት ምስክር ወረቀት ለማግኘት በሚቀርብ አቤቱታ ማናቸውም ያገባኛል የሚል ሰው ባል ወይም ሚስት አይደለም በማለት የሚያቀርበውን ተቃውሞና ክርክርን ይጨምራል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 75560 ቅጽ 17፣[14] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. አንቀጽ 80

(የአንድ ዳኛ የልዩነት ሀሣብ)

አንቀጽ ማገጣጠም”

1. የህጉን ዓላማና ግብ በጥልቀት ሳይፈትሹ ላይ ላዩን በማየት መተርጎም
2. የህብረተሰቡን ችግር የማይፈታ በተቃራኒው ችግር የሚፈጥር የህግ አተረጓጎም

“ተያያዣነት ያላቸው ነጥቦች በጥልቀት ሣይታዩ ሶስትና አራት የሚሆኑ የሕግ ድንጋጌዎች በማገጣጠም የሚሰጥ ውሣኔ ከችግር ፈችነቱ ይልቅ ችግር ፈጣሪነቱ የሚያመዝን እንደሚሆን ለመገንዘብ ይኸ[15] የህግ አተረጓጎም ከተሰጠ በኋላ እየተፈጠረ ያለውን የተመሠቃቀለ ሁኔታ በማየት በቂ ትምህርት ለመውሰድ ይቻላል፡፡”

ሰ/መ/ቁ. 34803 ቅጽ 8[16]

(የአንድ ዳኛ የልዩነት ሀሳብ)

ይርጋ መተው

አንድ ሰው የይርጋ ጊዜውን ትቶታል የሚባለው ለዕዳው ምንጭ የሆነውን ግዴታ በማመን
አዲስ መተማመኛ ሰነድ የሰጠ እንደሆነ ነው፡፡ ይርጋን መተው ውጤቱ ይርጋን የሚያቋርጥ ሳይሆን
አዲስ የይርጋ ጊዜ መቆጠር እንዲጀምር ያደርጋል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 90361 ቅጽ 6[17]

ድምር ውጤት የቅጣት አወሳሰን መርህ(የ—)

አንድ ሰው ሁለትና ከዚያ በላይ የሆኑ ተደራራቢ ወንጀሎችን ከፈጸመና
ወንጀሎቹ ነጻነትን በሚያሳጣ ቅጣት የሚያስቀጡ ከሆነ ለእያንዳንዱ ወንጀል
ሊቀጣ የሚገባውን ቅጣት በመደመር በወንጀለኛው ላይ የሚወሰነውን ቅጣት ለማስላት የሚያስችል የቅጣት አወሳሰን መርህ

ሰ/መ/ቁ. 92296 ቅጽ 17፣[18] ወንጀል ሕግ አንቀጽ 32(1) ሀ፣ 61(ሀ)፣ 65፣ 248(ለ)፣ 184(1) ለ፣ 187(1)፣ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁ. 652/2001 አንቀጽ 3 እና አንቀጽ 4

ጋብቻ

አንድ ወንድና ሴት ባልና ሚስት ሆነው አንድ ላይ ለመኖር የሚያደርጉት ሕጋዊ ስምምነት

በኢትዮጵያ ጋብቻ በሶስት ዓይነት መንገድ ሊፈፀም እንደሚችል የተሻሻለው የቤተሰብ ሕግ አንቀጽ 1 ያመለክታል፡፡ በነዚህ ስርዓቶች በአንደኛው ጋብቻ ከተፈፀመ በድጋሚ በሌላኛው ስርአት ሊፈጸም የሚገባበት የሕግ ምክንያት አይኖርም፡፡ ድጋሚ ተደርጎ እንኳን ቢገኝ ጋብቻው ፀንቶ የሚቆየው የመጀመሪያው ጋብቻ ከተደረገበት ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡ በአንድ ወንድና ሴት በመሃከል የሚደረግ ጋብቻ ፈርሶ እንደገና ካልተፈፀመ በቀር ጋብቻ አንድ እንጂ ሁለትና ከዚያ በላይ ሊሆን አይችልም፡፡

አንድ ወንድ እና ሴት ኢትዮጵያ ውስጥ ከተጋቡ በኋላ በድጋሚ በውጭ አገር ጋብቻ ቢፈጽሙ አንድ ጊዜ ጋብቻ ከተመሰረተ ሁለተኛ ጋበቻ የሚፈፀምበት የሕግ መሠረት የሌለ በመሆኑ ጋብቻው ውጤት የሚኖረው የመጀመሪያው ጋብቻ ከተፈፀመበት ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 40781 ቅጽ 8[19]

ጳጉሜ

እንደ አስራ ሦስተኛ ወር /እንደ ወር/ የማይቆጠር ጊዜ

ህጉ የይርጋ ጊዜውን በወር ወይም ወራት ከወሰነ ጊዜው የሚቆጠረው በጳጉሜ ውስጥ ያሉት ቀናት ታሳቢ ሳይደረጉ ነው፡፡

በፍትሐብሔር ህጉ ቁጥር 1860(3) በተመለከተው የጊዜ አቆጣጠር ደንብ መሰረት ጳጉሜ እንደወር አይቆጠርም፡፡ ጳጉሜ እንደ አስራ ሦስተኛ ወር የማትቆጠር መሆኑ ከታወቀና የሀገራችን የአንድ አመት ጊዜ 12 ወራቶች ከሆኑ ከዚህ አቆጣጠር ውጭ ያሉት ቀናት በተዋዋይ ወገኖች መካከል መብትም ሆነ ግዴታ ሊፈጥሩ አይገባም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 96458 ቅጽ 16፣[20] ፍ/ህ/ቁ. 1860(3)

ፈቃጅ የውል ህግ ድንጋጌዎች

ሰፊ ነፃነት ለተዋዋይ ወገኖች የሚሰጡ የውል ህግ ድንጋጌዎች

ተዋዋይ ወገኖች ህግ አውጭው በፈቃጅነት የደነገጋቸውን የውል ድንጋጌዎች መከተል ካልፈለጉ የመተው ነፃነት አላቸው፡፡ የፈቃጅ የህግ ድንጋጌዎች አለመሟላት በውሉ ህጋዊነት ላይ የሚያስከትለው ምንም አይነት ተጽዕኖ የለም፡፡ እነዚህ የህግ ድንጋጌዎች በተዋዋይ ወገኖች ፍላጎትና ፈቃድ ተጠቃሽና ተፈፃሚ የሚሆኑ ሲሆኑ ተዋዋይ ወገኖች በዝምታ ያለፉት ነገር ሲኖርና በዚያም ምክንያት ክፍተት ሲፈጠር ክፍተቱን ለመሸፈን ሊጠቀሱና ሊፈፀሙ የሚችሉ የህግ ድንጋጌዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ፈቃጅነት ያላቸው የውል ህግ ድንጋጌዎች የተዋዋዮቹን የመዋዋል ነፃነት (Freedom of contract) በማክበር ህግ አውጭው በአስገዳጅነት ሣይሆን በአማራጭነት የደነገጋቸው ናቸው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 34803 ቅጽ 8[21]

(የአንድ ዳኛ የልዩነት ሀሣብ)

ፍቺ

የሁለት ተጋቢዎችን የትዳር ግንኙት በሕግ መሠረት ማቋረጥ

ጋብቻ ከሚፈርስባቸው ምክንያቶች ውስጥ አንደኛው የፍቺ ውሣኔ ሲሰጥ መሆኑ የቤተሰብ ሕጉ አንቀጽ 75/ሐ/ ያመለክታል፡፡ ጋብቻ አንድ እንደሆነ ሁሉ ጋብቻው በፍቺ ሊፈርስ የሚችለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ሁለት የጋበቻ ስርአቶች መከናወናቸውም ሁለት ጊዜ የፍቺ ውሣኔ እንዲሰጥ ምክንያት ሊሆን አይችልም፡፡ ተጋቢዎቹ ግንኙታቸውን ማቋረጥ ከፈለጉ ጋብቻው በሁለት አይነት ስርአት ስለተፈፀመ ግንኙቱን ለማቋረጥ እያንዳንዱን ጋብቻ አስመልክቶ የፍቺ ውሣኔ ሊሰጥ የሚገባው አይሆንም፡፡ የሕጉም አላማ ይህ አይደለም፡፡

አንድ ወንድ እና ሴት ኢትዮጵያ ውስጥ ከተጋቡ በኋላ በድጋሚ በውጭ አገር ጋብቻ መስርተው በዛው አገር በፍርድ ቤት ፍቺ ከፈጸሙ በግራ ቀኙ መሐከል የነበረው ጋብቻ አንድ ብቻ በመሆኑ በውጭ አገር የተሰጠው የፍቺ ውሣኔ ይህን በመካከላቸው የነበረውን አንድ ጋብቻ እንዳፈረሰ ተደርጎ ሊቆጠር ይገባል፡፡ ግራ ቀኙ ውጭ አገር ከሄዱ በኋላ ሌላ የጋብቻ ሥነ ሥርዓት መፈፀማቸው ሁለት ትይዩ /Parallel/ ትዳር ውስጥ ነበሩ ሊያሰኛቸው አይችልም፡፡ በመሆኑም በመካከላቸው የነበረው የጋብቻ ግንኙነት አንድ የመሆኑን ያሕል የሚፈርሰውም በአንድ የፍቺ ውሣኔ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 40781 ቅጽ 8[22]

ፍቺ ሁኔታ(የ-)’ (Defacto divorce)

በራሱ ጊዜ የፈረሰ ጋብቻ

ከፍርድ ቤት ውሳኔ ውጪ በሆነ መንገድ በተግባር የተከናወነ ፍቺ (Defacto divorce)

ሰ/መ/ቁ. 61357 ቅጽ 13[23]

ፖሊስ አባል(የ—)

መሠረታዊ የሆነ የፖሊስ ሙያ ስልጠና ተሰጥቶት በኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ተቀጥሮ የሚሠራ የፌዴራል ፖሊስ አባል

በሕጉ የተቀመጡት ቅድመ ሁኔታዎች ሳይሟሉ አንድ ሰው የፖሊስ ቅጥር ፎርም የሚል ስያሜ የያዘ ሰነድ ስለሞላ ወይም በቅጥር ፎርሙ በሕጉ አግባብ የሚገኙት ማዕረጎች ተሰጥተውት የጥቅማ ጥቅሙ ተጋሪ መሆን እንደ ሕጉ አነጋገርና ይዘት ፖሊስ ነው ብሎ ትርጉም ለመስጠት አያስችልም፡፡

በኮንስታብል ማእረግ በመለዮ ለባሽነት ቅጥር ፈጽሞ በፖሊስ ሆስፒታል ውስጥ ሲያገለግል የነበረ ሐኪም ለፖሊስነት የሚያበቁትን የምልመላና የፖሊሳዊ ስልጠና ወስዶ ቃለ መሀላ ፈጽሞ በአባልነት ካልተመዘገበ በስተቀር የፖሊስ አባል አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 99367 ቅጽ 16፣[24] የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ ቁ. 720/2004 አንቀጽ 2(1)፣ 14፣ የፌደራል ፖሊስ  አባላት መተዳደሪያ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁ. 268/2005 አንቀጽ 5(1)፣ 6(1)፣ 7(1)

 

[1] አመልካች ወ/ሮ ልዩሴት ሥዩም እና ተጠሪ አቶ ሸዋፈራ ንጉሴ ሚያዝያ 12 ቀን 2007 ዓ.ም. በተጨማሪ አመልካች የወ/ሮ ብሬ አያና ወራሾች /እነ አሰገደች በቀለ/ 4 ሰዎች/ እና ተጠሪዎች እነ ዓለማየሁ አየለ /6 ሰዎች/ ሰ/መ/ቁ. 36ዐ6ዐ ሚያዝያ 29 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም ያልታተመ ይመለከቷል፡፡

[2] አመልካች ዳንኤል ዘሚካኤል እና ተጠሪ ቢሃሪ ባቡላል ሞዲ ሰኔ 21 ቀን 2005 ዓ.ም.

[3] አመልካች ቱሌን ዩኒቨርሲቲ አሲስታንስ ፕሮግራም ኢትዮጵያ እና ተጠሪ ዶ/ር ዮዲት አብርሃም መጋቢት 22 ቀን 2006 ዓ.ም.

[4] አመልካች የሐረር (ደ/ሳ) ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን እና ተጠሪዎች ወ/ሮ ማንያህልሻል አበራ መጋቢት 13 ቀን 2005 ዓ.ም.

[5] አመልካቾች እነ የሻረግ መንግሥቱ እና ተጠሪ እማሆይ የሻረግ ፈረደ ታህሣስ 17 ቀን 1998 ዓ.ም.

[6] አመልካች ብራንድ ኒው የቴክኒክና ሙያ ማሠልጠኛ ማዕከል ኃ/የተ/የግ/ማኀበር እና ተጠሪ አቶ መስፍን ታደሰ ግንቦት 18 ቀን 2001 ዓ.ም.

[7] የኢትዮጵያ መድን ድርጅት እና ተጠሪ ባሌ ገጠር ልማት ድርጅት መጋቢት 11 ቀን 2004 ዓ.ም.

[8] አመልካች መ/ር መኳንንት ወረደ እና ተጠሪዎች የእነ መስከረም ዳኛው /4 ሰዎች/ ሞግዚት አቶ ጥጋቡ መኮንን ጥቅምት 27 ቀን 2001 ዓ.ም.

[9] አመልካች ወ/ሮ አስረስ መስፍን እና ተጠሪ ወ/ሮ ውብነሽ ታከለ ጥቅምት 28 ቀን 2000 ዓ.ም.

[10] አመልካቾች እነ ወ/ት ፍሬወይኒ አለም /3 ሰዎች/ እና ተጠሪ አቶ አለም መሐሪ ግንቦት 23 ቀን 2005 ዓ.ም. በተጨማሪ አመልካቾች የእነ ህጻን ሲኢድ ዘውዴ /3 ሰዎች/ ሞግዚት እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ ጥሩሰው ሞሳ /9 ሰዎች/ ሰ/መ/ቁ. 94713 ቅጽ 17 መጋቢት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ይመለከቷል፡፡

[11] አመልካች ወ/ሮ አለሚቱ አግዛቸው እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ ዝናሽ ኃይሌ ሚያዝያ 18 ቀን 1999 ዓ.ም.

[12] አመልካች እነ ሴንትራል ቬኑ ኃላፉነቱ የተወሰነ የግል ማህበር /4 ሰዎች/ እና ተጠሪዎች እነ አቶ ሰለሞን ከተማ /2 ሰዎች/ ጥር 3 ቀን 2004 ዓ.ም.

[13] አመልካች አቶ ሽብሩ ጌቱ ሴንጫ እና ተጠሪ የፌዴራል አቃቤ ሕግ መጋቢት 28 ቀን 2007 ዓ.ም.

[14] አመልካች ወ/ሮ ኪሮስ ገ/ማሪያም እና ተጠሪ አቶ ገብረ ስላሴ ሃይሌ ሐምሌ 26 ቀን 2004 ዓ.ም.

[15] በሰ/መ/ቁ. 34803 የተሰጠውን የህግ አተረጓም ይጠቅሳል፡፡

[16] አመልካች መ/ር መኳንንት ወረደ እና ተጠሪዎች የእነ መስከረም ዳኛው /4 ሰዎች/ ሞግዚት አቶ ጥጋቡ መኮንን ጥቅምት 27 ቀን 2001 ዓ.ም.

[17] አመልካቾች እነ ወ/ሮ አለዊያ ዑመር /7 ሰዎች/ እና ተጠሪ አቶ ሐሺም ሁሴን የካቲት 26 ቀን 2006 ዓ.ም.

[18] አመልካቾች እነ አንዱዓለም አራጌ (3 ሰዎች) እና ተጠሪ የፌደራል ዓቃቤ ህግ

[19] አመልካች አቶ ፍቅረሥላሴ ካህሳይ እና ተጠሪ ወ/ሮ ሮማን ታደሰ ሐምሌ 3ዐ ቀን 2001 ዓ.ም.

[20] አመልካች ኢትዮጵያ የርቀት ትምህርት ኮሌጅ እና ተጠሪ ዶ/ር ደሣለኝ ተመስገን ሐምሌ 29 ቀን 2006 ዓ.ም.

[21] አመልካች መ/ር መኳንንት ወረደ እና ተጠሪዎች እነ መስከረም ዳኛው /4 ሰዎች/ ጥቅምት 27 ቀን 2001 ዓ.ም.

[22] አመልካች አቶ ፍቅረሥላሴ ካህሳይ እና ተጠሪ ወ/ሮ ሮማን ታደሰ ሐምሌ 3ዐ ቀን 2001 ዓ.ም.

[23] አመልካች አቶ ፍቅሬስላሴ እሽቴ እና ተጠሪ ወ/ሮ ዋጋዬ ጋይም ሕዲር 22 ቀን 2004 ዓ.ም.

[24] አመልካች ዶ/ር ሕሊና ፍቅሬ እና ተጠሪ የፌዴራል ፖሊስ ሆስፒታል ሐምሌ 29 ቀን 2006 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment, law, Uncategorized

ማጣቀሻዎች እና ህግ አተረጓጎም

$
0
0

ማጣቀሻዎች እና ህግ አተረጓጎም

በህግ የተደነገጉ ወይም በልማድ የዳበሩ የህግ አተረጓጎም ስልቶችን በመጠቀም አግባብነት ያለውን የህግ ትርጉም ማበጀት አስቸጋሪ በሚሆንባቸው ሁኔታዎች ከተጻፈው ህግ ወጣ ብሎ አግባብነት ያላቸውን ምንጮች መዳሰስ ጥሩ አማራጭ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ በተለያዩ አገራት የሚገኙ ፍርድ ቤቶች ውጫዊ ማጣቀሻዎችን /Extrinsic Aids/ የመጠቀም ፍላጎታቸውና ልማዳቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ መጨመር አሳይቷል፡፡[1] በስፋት ተቀባይነት ካገኙ ማጣቀሻዎች መካከል ሐተታ ዘምክንያት፣ /Legislative History/ የህጉ ታሪካዊ ዑደት /Legislative Evolution/ ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች፣ /International Agreements/ የሌሎች አገራት ህግ እና የፍርድ ቤት ውሳኔዎች እንዲሁም የምሁራን ስራዎች ሰፊ ተቀባይነት አግኝተዋል፡፡[2]

የፌደራሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በበርካታ መዝገቦች በማጣቀሻ የታገዙ ውሳኔዎች ሰጥቷል፡፡ በእርግጥ ጥቅም ላይ የዋሉበት መንገድ ሲታይ ግልጋሎታቸው እንደ ደጋፊ ማለትም እንደ ማጠናከሪያ ምክንያት ነው፡፡ የሚጠቀሱት ምንጮች አከራካሪ የህግ ጭብጦችን ለመፍታት ቀጥተኛ አስተዋጽኦ አላደረጉም፡፡ ሁሉንም ውሳኔዎች ማካተት ባይቻልም በተወሰኑት ላይ የተደረገው ከፊል ዳሰሳ እንደሚከተለው ይቀርባል፡፡

የሌሎች አገራት ተሞክሮና ልምድ

የአገራችን የተጠናቀሩ ህጎች የተለያዩ አገራት ህጎች አሻራ አርፎባቸዋል፡፡ የአንድ የህግ ክፍል ለምሳሌ የውል ህግ ወይም ከውል ውጪ ኃላፊነት ህግ በስራቸው የተካተቱት ዝርዝር ድንጋጌዎች ሳይቀር ምንጫቸውን ለማወቅ አዳጋች አይደለም፡፡ ከዚህ አንጻር ፈታኝ ሁኔታ ሲፈጠር ህጉ የተቀዳበትን አገር የህግ ስርዓትና የፍርድ ቤት ውሳኔዎች በማጣቀሻነት መጠቀም የአገራችንን የህግ አተረጓጎም በእጅጉ ያጎለብተዋል፡፡ በዚህ ደረጃ ጠለቅ ያለ ፍተሻ የተደረገባቸው መዝገቦች ባይኖሩም በጥቅል አገላለጽ “ሌሎች አገራት” “በርካታ አገራት” “የዳበረ የህግ ስርዓት ያላቸው አገራት” ወዘተ…በሚል ማጣቀስ በስፋት ይስተዋላል፡፡ ለአብነት ያክል በሁለት መዝገቦች የሰፈረውን ገለጻ እናያለን፡፡

ሰበር መ/ቁ/ 23632 ቅጽ 5 አመልካች ወ/ት ፀዳለ ደምሴ እና ተጠሪ አቶ ክፍሌ ደምሴ ጥቅምት 26 ቀን 2000 ዓ.ም.

እንደሚታወቀው የልጆቻቸውን መብትና ደህንነት በማስጠበቅ ረገድ ከወላጆቻቸው የበለጠ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ሰው ሊኖር ስለማይችል ሕግ አውጭው
በመርህ ደረጃ የተቀበለው በመሆኑ በሕይወት ያለው አባት ወይም እናት የሕፃን ልጁ ሞግዚት እና አስተዳዳሪ አድርጎ የመሾሙ አሠራር አገራችንን ጨምሮ
የበርካታ አገራት ተሞክሮ መሆኑ ይታወቃል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 14981 ቅጽ 12 አመልካች የኢትዮጵያ ልማት ባንክ እና ተጠሪ ወ/ሮ ሃዋ መሐመድ ግንቦት 04 ቀን 1998 ዓ.ም.

በአገራችን ራሱን የቻለ የማስረጃ ሕግ ባለመኖሩ በዚህ ጉዳይ በቀጥታ ተፈፃሚነት ያለው ድንጋጌ ሊጠቀስ ባይችልም በሌሎች አገሮች ተቀባይነት ካገኘው
የማስረጃ ሕግ መርህ ግን መረዳት የሚቻለው የባለሙያ አስተያየት ብቻውን ለመቆም የሚችል ወይም በተቃራኒ ማስረጃ ሊስተባበል የማይችል ሳይሆን
ይልቁንም ከሌሎች ማስረጃዎች ጋር ተገናዝቦ ብቃቱና ተአማኒነቱ ሊመዘን የሚገባ መሆኑን ነው፡፡

በሁለት መዝገቦች ላይ ደግሞ እስራኤል እና ሩስያ በስም ተለይተው ተጠቅሰዋል፡፡

ሰ/መ/ቁ.112091 ቅጽ 18 አመልካች አንድነት ለፍትህና ለዱሞክራሲ ፓርቲ እና ተጠሪዎች ሠማያዊ ፓርቲ ሚያዝያ 28 ቀን 2007 ዓ.ም.

በምርጫ ወቅትና ከተመረጡ በኋላ የፓለቲካ ድርጅቶች አባላት የሚፈጽሙትን የክደት ተግባር ለመቆጣጠርና ለማስቀረት የዳበረ ዲሞክራሲ ሥርዓት ያላቸው
እንደ እስራኤል ያሉ ሌሎች አገሮች በሕገ መንግስታቸውና በሌሎች የሕግ ማዕቀፍች ከልካይ የሆኑና ይህንን ተግባር በሚፈፅሙ ላይ ተጠያቂነት የሚያስከትሉ
የህግ ድንጋጌዎችን በመደንገግ ተግባራዊ አድርገዋል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 44561 ቅጽ 10 አመልካች ወ/ሮ ገነት በላይ እና ተጠሪ አቶ ፈኔት ተክሉ /ሞግዚት/

በርካታ አገሮች ለምሣሌ ሩስያ ከሟች ወደ ወራሾች በውርስ ሊተላለፉ የሚችሉ ንብረቶችና መብቶች በዝርዝር ያስቀምጣሉ፡፡

የምሁራን ስራዎች

ከውል ውጭ የሚደርስ ኃላፊነት ሕጎች ግቦችን በተመለከተ በሶስት መዝገቦች[3] ላይ የፕሮፌሰር ጆርጅ ቺቺኖቪች The Ethiopian law of compensation for damages መጽሐፍ በምንጭነት ተጠቅሷል፡፡

በሶስቱም መዝገቦች ላይ የፕሮፌሰር ጆርጅ ቺቺኖቪች ስራ የተጠቀሰው በተመሳሳይ ነጥብ ላይ ነው፡፡ ስለሆነም በሰ/መ/ቁ. 35034 ቅጽ 9 የሰፈረውን ገለጻ ማየቱ ይበቃል፡፡

በፍትሐብሔር ሕጋችን ከውል ውጪ አላፊነትን በሚመለከት የተቀመጡ ድንጋጌዎች ጉዳት የደረሰበት ሰው የሚካስበትን ሥርዓት የዘረጉ ናቸው፡፡
የእነዚህ ድንጋጌዎች ዓይነተኛ ግባቸውም ጉዳትን የመካስና የጥፋት ባህርይን የመግታት ስለመሆኑ በድንጋጌዎቹ ላይ ማብራሪያ ጽሑፍ ያበረከቱት
በቀድሞ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ዩኒቨርስቲ የሕግ ትምህርት ክፍል አስተማሪ የነበሩት ጆርጅ ቺቺኖቪች ገልፀውታል፡፡

በሶስቱም መዝገቦች ላይ የምሁራ ስራ ለውሳኔ መነሻ የሚሆን ግንዛቤ ከማስጨበጥ የዘለለ ፋይዳ አልነበረውም፡፡ ለአከራካሪ የህግ ጭብጥ ቀጥተኛ አስተዋጽኦ በማድረግ ምሁራዊ ስራ እንደ ህግ ትርጉም ዕውቅና ያገኘው ሮበርት አለን ሴድለር “Ethiopian civil procedure” በሚል ርእስ ያዘጋጁት መጽሐፍ ሲሆን ምሁሩ ለክስ ምክንያት የሰጡት ፍቺ በችሎቱ ዘንድ ሙሉ ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ ችሎቱ የምሁሩን ስራ በምንጭነት ሲጠቅስ እንዳመለከተው፤

ሮበርት አለን ሴድለር "Ethiopian civil procedure" በሚል ርእስ ባዘጋጁት መጽሀፍ ላይ "የክስ ምክንያት" አለ ብሎ ለመወሰን የሚቻለው በክሱ ላይ የቀረበው
ነገር ቢረጋገጥ ከሣሹ የጠየቀውን ዳኝነት ለማግኘት ሕግ ይፈቅደሉታል ወይ? ለሚለው ጥያቄ አዎንታዊ ምላሽ መስጠት ሲቻል እንደሆነ ገልፀዋል፡፡[4]

ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች

ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች በኢትዮጵያ የህግ ስርዓት በተለይም በፍርድ ቤቶች ዘንድ ያላቸው ቦታ አናሳ ነው፡፡ ለተፈጻሚነታቸው ውስንነት ምክንያት ከሆኑት መካከል ከእንግሊዝኛ ወደ አማርኛ እና ሌሎች የክልል የስራ ቋንቋዎች አለመተርጎማቸው እንዲሁም በቀላሉ ሊገኙ አለመቻላቸው በዋነኛነት ይጠቀሳሉ፡፡ በተጨማሪም በበታች ፍ/ቤቶች የሚስተዋለው የመዝገብ መጨናነቅ ከተጠቀሱት ምክንያቶች ጋር ተደማምሮ ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶችን በውሳኔ አሰጣጥ ሂደት የመጠቀም ልማድ አመንምኖታል፡፡

የሰበር ችሎት የአገሪቱ የመጨረሻው የዳኝነት አካል እንደመሆኑ መሰረታዊ በሆኑ ጉዳዮች ላይ የሚነሱ የህግ ጭብጦች አገራዊ ብቻ ሳይሆን ዓለም ዓቀፋዊ ገፅታቸውን ጭምር በጥልቀት መዳሰስ ይኖርበታል፡፡ ይህም ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች በችሎቱ ዘንድ የተለየ ትኩረት እንዲያገኙ ያደርጋቸዋል፡፡ በአንጻራዊነት ሲታይ ከላይ የተጠቀሱት ችግሮቹ በሰበር ችሎት ጎልተው አይታዩም፡፡ ስለሆነም በስር ፍ/ቤት ውሳኔዎች ላይ ደብዛቸው የማይታየው ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች በሰበር ችሎት አልፎ አልፎ መጠቀሳቸው ብዙም የሚገርም አይሆንም፡፡

በህግ አተረጓጎም ሂደት የዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች ሚና በተመለከተ የሰበር ችሎት በሰ/መ/ቁ 44101 ቅጽ 10 (አመልካች ሚስስ ፍራንሱዊስ ፖስተር እና ተጠሪ እነ ሚስተር ዱከማን ቬኖ (2 ሰዎች) የካቲት 24 ቀን 2002 ዓ.ም.) በሐተታው እንዳሰመረበት ኢትዮዽያ ያፀደቀቻቸው የዓለም አቀፍ ስምምነቶች የአገሪቱ የሕግ አካል መሆናቸውን በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ሕገ-መንግሥት በአንቀጽ 9(4) ስር የተደነገገ ሲሆን በሕገ መንግሥቱ በስፋት ሽፋን የተሰጣቸው መሠረታዊ የመብቶችና የነጻነቶች ድንጋጌዎች ሀገሪቱ ከተቀበለቻቸው ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች ሕግጋትና ስምምነቶች ጋር በተጣጣመ መንገድ መተርጎም ይኖርባቸዋል፡፡ አለመጣጣሙ የሚፈታበት መንገድ ግን አሁንም ድረስ ቁርጥ ያለ ምላሽ አላገኘም፡፡

በሰበር ችሎት በተደጋጋሚ የሚጠቀሱ ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች በቁጥር ውስን ናቸው፡፡ ለምሳሌ ያህል፤

  • ዓለም አቀፍ የሲቪል እና የፖለቲካ መብቶች ቃል ኪዳን ስምምነት[5]
  • የአፍሪካ የሰዎችና የህዝቦች መብት ቻርተር[6]
  • የአፍሪካ ሕፃናት መብቶችና ደህንነት ቻርተር[7]
  • የሕፃናት መብቶች ኮንቬንሽን[8]
  • ዓለም ዓቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ድንጋጌ /The Universal Decleration of Human Rights)[9]

ከእነዚህ በተጨማሪ የሚከተሉት ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች አከራካሪውን የህግ ጭብጥ ለመፍታት በቀጥታ ተፈጻሚ ተደርገዋል፡፡

  • የዓለም የፖስታ ሕብረት ስምምነት /ኮንቬንሽን/[10]
  • የተባበሩት መንግስታት ቻርተር[11]

[1] Ruth Sullivan, Statutory Interpretation, (2nd, Toronto: Irwin Law Inc., 2007) ገፅ 279

[2] ዝኒ ከማሁ ገፅ 279-302

[3] ሰ/መ/ቁ. 19338 ቅጽ 5 አመልካች ዘይነባ ሐሰን እና ተጠሪ ፍሬው ተካልኝ መጋቢት 2 ቀን 2000 ዓ.ም. ፣ ሰ/መ/ቁ. 34138 ቅጽ 5 አመልካቾች እነ ሲስተር ገነት ጌታቸው /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ ወንድወሰን ኃይሉ ወልደማርያም ግንቦት 26 ቀን 2000 ዓ.ም. እና አመልካቾች እነ ወ/ሮ ጥሩቀለም ደሴ እና ተጠሪዎች እነ ወ/ሮ ጽጌ ከፍያለው ጥቅም ዐ6 ቀን 2ዐዐ1 ዓ

[4] ሰ/መ/ቁ. 16273 ቅጽ 2 አመልካች የኢት/ቴሌኮሙኒኬሽነ ኮርፖሬሽን እና ተጠሪ አቶ ገንታ ገምአ ጥቅምት 22/98 ዓ.ም.

[5] ሰ/መ/ቁ. 73514 ቅጽ 14 አመልካች ተስፋዬ ጡምሮ እና ተጠሪ የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ዐቃቤ ህግ ህዳር 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

[6] ሰ/መ/ቁ. 42150 ቅጽ 12 አመልካች የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ እና ተጠሪዎች እነ አቶ ዲንኤሌ ካሣ /ሃያ ሁለት ሰዎች/ ጥቅምት 29 ቀን 2003 ዓ.ም. በልዩነት ሀሳብ የተጠቀሰ

[7] ሰ/መ/ቁ. 35710 ቅጽ 8 አመልካች ወ/ሮ እፀገነት እሸቱ እና ተጠሪ ወ/ሮ ሰላማዊት ንጉሴ ታህሣሥ 16 ቀን 2001 ዓ.ም.

[8] ዝኒ ከማሁ

[9] ሰ/መ/ቁ 57632 ቅጽ 12 አመልካች ሰማኸኝ በለው እና ተጠሪ የፌደራል ዐቃቤ ህግ ታህሳስ 25 ቀን 2003 ዓ.ም.

[10] ሰ/መ/ቁ. 24173 ቅጽ 5 አመልካች የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅት እና ተጠሪ ወ/ሮ አይዳ ሐሰን ጥቅምት 21 ቀን 2000 ዓ.ም.

[11] ሰ/መ/ቁ/ 98541 ቅጽ 17 አመልካች አቶ አለማየሁ ኦላና እና ተጠሪ የተባበሩት መንግስታት የልማት ድርጅት (UNDP) ህዳር 10 ቀን 2007 ዓ.ም.


Filed under: Articles

የህግ ትርጉም መለወጥ እና ተለውጧል ስለሚባልበት ሁኔታ

$
0
0

የህግ ትርጉም መለወጥ

የህግ ትርጉም አስገዳጅነቱ ለስር ፍ/ቤቶች እንጂ ለራሱ ለችሎቱ አይደለም፡፡ ችሎቱ በሌላ ጊዜ በተመሳሳይ ጭብጥ የተለየ አቋም ሊይዝ ይችላል፡፡ የትርጉም መለወጥ በጠባቡ ካልተተገበረ በስር ፍርድ ቤቶች ዘንድ ሊኖረው የሚገባውን የተሰሚነትና የተቀባይነት ደረጃ በእጅጉ ያሳንሰዋል፡፡ መረሳት የሌለበት ነገር ወጥነት ለበታች ፍ/ቤቶች ብቻ ሳይሆን ለራሱ ለችሎቱም በእጅጉ ያስፈልገዋል፡፡ በአንድ ጭብጥ ላይ በየጊዜው የሚቀያየር የህግ ትርጉም ተቀባይነቱ አጠያያቂ ነው፡፡ ወዲያው ወዲያው አቋም ሲለዋወጥ ፍርድ ቤቶችን ያደናግራል፡፡

በተመሳሳይ ጭብጥ የተለየ ትርጉም መስጠት እጅግ አስፈላጊ የሚያደርጉ ሁኔታዎች ወይም ምክንያቶች መኖራቸው እስካልተረጋገጠ ድረስ በአንድ ወቅት የተሰጠ ትርጉም ፀንቶ ሊቆይ ይገባል፡፡ የተለየ ትርጉም ሲያስፈልግ ለውጥ ማድረግ የተፈለገበትን ምክንያት በአዲሱ ውሳኔ ላይ በግልጽ ማመልከትና የበፊቱን ውሳኔ በማያሻማ መልኩ በግልጽ መሻር ያስፈልጋል፡፡ በግልጽ የሚደረግ የትርጉም ለውጥ ያልተገባ ውዥንብርን ያስወግዳል፡፡ በአነስተኛ ወጪ ፍትሕ በቀላሉ እንዲሰፍንም ያደርጋል፡፡

የቀድሞ የህግ ትርጉም በግልጽ ቀሪ ተደርጎ አዲስ አቋም ከተያዘባቸው መዝገቦች መካከል ሰ/መ/ቁ 42239 ቅጽ 10፣[1]  43821 ቅጽ 9[2]  እና 36730 ቅጽ 9[3] ተጠቃሽ ናቸው፡፡ በሰ/መ/ቁ 42239 የግልግል ዳኝነት ጉባኤ የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻ እንዲሆን ስምምነት ከተደረገ በሰ/ችሎት ሊታይ አይችልም በማለት በሰ/መ/ቁ 21849 ተሰጥቶ የነበረው የህግ ትርጉም ተሽሯል፡፡ በተለወጠው ትርጉም መሰረት የጉባዔው ውሳኔ በሰበር ስልጣን ስር እንዲወድቅ ተደርጓል፡፡ በሰ/መ/ቁ 43821 ዳኝነት እንደገና እንዲታይ ጥያቄው መቅረብ ያለበት ከይግባኝ በፊት እንደሆነ በሰ/መ/ቁ 16624 ተሰጥቶ የነበረው የህግ ትርጉም ተለውጦ ከይግባኝ በኋላም ሊቀርብ እንደሚችል አቋም ተይዞበታል፡፡ የሰመ/ቁ 36730 የይርጋ ማቋረጫ ምክንያትን የሚመለከት ሲሆን ከዚህ ቀደም በሰ/መ/ቁ 16648 ስልጣን ለሌለው የዳኝነት አካል ክስ ማቅረብ የይርጋ ጊዜን እንደማያቋርጥ ተደርጎ ህጉ መተርጎሙ አግባብነት እንደሌለው ታምኖበት የቀድሞው ትርጉም ተቀይሯል፡፡

ሶስቱም መዝገቦች ውሳኔ ያገኙት ሰባት ዳኞች በተሰየሙበት ችሎት ነው፡፡ ይህም የትርጉም ለውጥ ከሚደረግበት ስርዓት ጋር በተያያዘ ጥያቄ እንድናነሳ ያስገድደናል፡፡ ሰባት ዳኞች በተሰየሙበት ችሎት የተሰጠ የህግ ትርጉም ከሰባት ያነሱ ለምሳሌ አምስት ዳኞች በተሰየሙበት ችሎት ሊለወጥ ይችላል? የዳኞች ቁጥር እንደተጠበቀ ሆኖ በሙሉ ድምጽ የተሰጠ ውሳኔ በአብላጭ ድምጽ ሊለወጥ የመቻሉ ጉዳይም ሌላው በጥያቄነት መነሳት ያለበት ነው፡፡

የህግ ትርጉም ተለወጠ ስለሚባልበት ሁኔታ

የህግ ትርጉም ተለውጧል የሚባለው በግልፅና በማያወላዳ አነጋገር የቀድሞው ትርጉም ተሽሮ በአዲስ ሲተካ ነው፡፡ በዚህ መልኩ ለውጥ የተደረገባቸው የሰበር ውሳኔዎች በቁጥር ኢምንት ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ ግልፅ የሆነ አነጋገር በሌለበት በበርካታ መዝገቦች የሰበር ችሎት አቋሙን ቀይሯል፡፡ በዚህ መልኩ በዝምታ የሚደረግ ለውጥ በቁጥር እየበዙ ለመጡት የሚጋጩ ውሳኔዎች መፈጠር ምክንያት ሆኗል፡፡ የግጭት መኖር ከትርጉም መለወጥና አስገዳጅነት ጋር ተያይዞ መሰረታዊ ጥያቄ ያስነሳል፡፡ ለዚህ አንገብጋቢ ጥያቄ አሁንም ድረስ በችሎቱ ሆነ በህግ አውጪው መላ አልተዘየደለትም፡፡

ከግጭት ባሻገር የትርጉም መለወጥ መኖሩን ለመረዳት አደናጋሪ የሆነባቸው ሁኔታዎች ተከስተዋል፡፡ ሁኔታዎቹ የስር ፍ/ቤትን አደናግረው ፍትሕ ፈላጊውን ዜጋ ላልተገባ መንገላታት ዳርገውታል፡፡

ውርስ እንዲጣራ የሚቀርብ አቤቱታ ለማየት የዳኝነት ስልጣን የተሰጣቸው ፍርድ ቤቶችን አስመልክቶ በሰበር ችሎት የተፈጠረ ድንገተኛ ስህተት ተጠቃሽ የችግሩ ማሳያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡

በሰ/መ/ቁ. 35657 ቅጽ 9[4] እና በሌሎችም መዝገቦች የአዲስ አበባ ፍርድ ቤቶች የውርስ ይጣራልኝ አቤቱታን ለመቀበልና ለመዳኘት ስልጣን እንደሌላቸው ተመልክቷል፡፡ ሆኖም በሰ/መ/ቁ. 36205 እነዚህ ፍርድ ቤቶች የውርስ ማጣራት አቤቱታ በማስተናገዳቸው መሰረታዊ የህግ ስህተት ተፈጽሟል የሚል አቤቱታ ለሰበር ችሎት ቀርቦ ችሎቱ ግን አቤቱታውን ባለመቀበል የስር ፍ/ቤቶችን ውሳኔ አጽንቶታል፡፡ ይህም በአንድ ጉዳይ ላይ በይዘታቸው የማይጣጣሙ ሁለት ውሳኔዎች መፈጠር ምክንያት ሊሆን ችሏል፡፡

በማይጣጣሙ ውሳኔዎች የተነሳ በአንድ በኩል የአዲስ አበባ ፍ/ቤቶች በሰ/መ/ቁ. 35657 የተሰጠውን የህግ ትርጉም ዋቢ እያደረጉ በሌላ በኩል የፌደራል ፍርድ ቤቶችም በሰ/መ/ቁ. 36205 የተሰጠውን ውሳኔ እያጣቀሱ የውርስ ማጣራት አቤቱታ ለማየት ፈቃደኛ ሳይሆኑ በመቅረታቸው ተመሳሳይ አቤቱታዎች ወደ ሰበር መጉረፍ ጀመሩ፡፡[5]

በሰ/መ/ቁ. 52530 ቅጽ 11፣ በሰ/መ/ቁ 44750 ያልታተመ፣ በሰ/መ/ቁ. 35657 ቅጽ 9 እና በሌሎች ተመሳሳይ የሰበር ውሳኔዎች ውርስ ማጣራት የፌደራል ፍ/ቤቶች የዳኝነት ስልጣን እንደሆነ ወጥ አቋም ቢያዝበትም ችሎቱ በሰ/መ/ቁ. 36205 ስህተት መስራቱን አምኖ ማስተካከያ ወይም ማሻሻያ አላደረገም፡፡ ከዚያ ይልቅ የሰ/መ/ቁ. 35657 የህግ ትርጉም በሰ/መ/ቁ. 36205 አለመለወጡ በተደጋጋሚ እየተገለጸ የችግሩን ምንጭ ወደ ስር ፍ/ቤቶች የማሸሽ አዝማሚያ ታይቷል፡፡ ችሎቱ ስህተቱን በከፊል በማመን ዕውቅና የሰጠው በሰ/መ/ቁ 52892 ያልታተመ[6] ነው፡፡ በዚህ መዝገብ የስር ፍ/ቤትን ውሳኔ ማጽናት በህግ አስገዳጅነት ሆነ በትርጉም መለወጥ ረገድ የሚኖረው ውጤት የችሎቱን ትኩረት ሳያገኝ በዝምታ ታልፏል፡፡ በተቃራኒው በሰ/መ/ቁ. 36205 የስር ፍ/ቤት ውሳኔ የጸናበት መንገድ ከሌላው ‘ማጽናት’ እንደሚለይ ማስተባበያ የሚመስል ማብራሪያ ቀርቧል፡፡ ይዘቱ እንደሚከተለው ይነበባል፡፡

“…በዚህ ረገድ ይህ ሰበር ችሎት በበርካታ መዝገቦች ላይ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ ለውሳኔው መሠረት ያደረገው የአ/አ ከተማ ፍርድ ቤቶች ሥልጣን በአዋጅ 408/96 ላይ
 ስለወራሽነት ማስረጃ የመስጠት ሥልጣን በተመለከተ የተደነገገው ቢኖርም የውርስ ማጣራት ተግባር ሊያስከትል ከሚችለው ውስብስብ የሕግ ጥያቄ አንፃር በተለየ
 ሁኔታ መታየት እንዳለበት በማገናዘብ ይህ ጥያቄ በቀረበ ጊዜ መታየት ያለበት በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት ሊሆን ይገባል ሲል በሰበር መ/ቁ 35657 ትርጉም
 ሰጥቷል፡፡ ከዚህ በተለየ ሁኔታ ግን የአ/አ ከተማ ፍ/ቤት ሰበር ችሎት የሰጠው ውሳኔ በሰበር ሰሚ ችሎት አስቀርቦ ካከራከረ በኋላ ስሕተት የለውም ተብሎ የዚህ
ፍ/ቤት ሰበር መ/ቁ 36205 ውሳኔው መፅናቱ ይታወሳል፡፡ በኋለኛው መዝገብ የተሰጠው ውሳኔ በፎርም ብቻ የፀና በመሆኑ የቀድሞውን የሰበር አቋም የለወጠ
ስለመሆኑ አመልካች ምክንያት አልተሰጠበትም፡፡” (ሰረዝ የተጨመረ)

በፎርም ብቻ ማጽናት? በፎርም ሆነ ያለ ፎርም ሰበር ያጸናው የስር ፍ/ቤት ውሳኔ ለተከራካሪ ወገኖች መብት ይፈጥራል፡፡ ግዴታ ያቋቁማል፡፡ በየትኛውም መልኩ ቢሆን የማጽናት ውሳኔ ለስር ፍ/ቤቶች የህግ ትርጉም ይሁንታ ይሰጣል፡፡ ስለሆነም የሰበር ችሎት መሰረታዊ የህግ ስህተት እንዳልተሰራ ማረጋገጫ እየሰጠ የስር ፍ/ቤቶች ተቃራኒ አቋም ማንጸባረቅ አይችሉም፡፡ የስር ፍርድ ቤት ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት ቢፈጸምበትም ባይፈጸምበትም ለችሎቱ ውሳኔ መሰረት የሆነውን የህግ ትርጉም አስገዳጅነት አያስቀረውም፡፡

 

[1] አመልካች ብሔራዊ ማዕድን ኮርፖሬሽን ኃላ.የተ. የግል ኩባንያ እና ተጠሪ ዳኒ ድሪሊንግ ኃላ.የተ. የግል ኩባንያ ጥቅምት 29 ቀን 2003 ዓ.ም.

[2] አመልካች ወ/ሮ ትርሐስ ፍስሐዬ እና ተጠሪ ወ/ሮ ዘነበች በሪሁን ጥር 5 ቀን 2002 ዓ.ም.

[3] አመልካች የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን እና ተጠሪ አቶ አማረ ገላው ሐምሌ 30 ቀን 2002 ዓ.ም.

[4] ጥቅምት 13 ቀን 2001 ዓ.ም. አመልካቾች እነ ወ/ሮ እመቤት መክብብ እና ተጠሪ አቶ በድሉ መክብብ

[5] ለምሳሌ ሰ/መ/ቁ. 52530 ቅጽ 11 ኀዳር 14 ቀን 2003 ዓ.ም. አመልካች እነ አቶ ሰናይ ልዑልሰገድ /2 ሰዎች) እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ ትእግስት ኃይሌ እና ሰ/መ/ቁ 44750 ያልታተመ አመልካች አቶ መለሰ ደጀኑ እና ተጠሪ ወ/ሮ ወይንሸት ታደሰ መጋቢት 07 ቀን 2002 ዓ.ም. ይመለከቷል፡፡

[6] አመልካች ወ/ሮ ብዙነሽ ዘለቀ እና ተጠሪዎች እነ ወ/ሮ አሰገደች ጥላሁን /2 ሰዎች/ ሐምሌ 26 ቀን 2002 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

በአሉታ ማመዛዘን -ክፍል 1

$
0
0

ያልተከለከለ ሁሉ የተፈቀደ ነው? ያልተፈቀደ ሁሉ የተከለከለ ነው? ጀማሪ የህግ ተማሪዎች እንዲሁም በህግ ሙያ ያልተሰማሩ ሰዎች በእነዚህ ጥያቄዎች ላይ የጦፈ ክርክር ሲገጥሙ ማየት የተለመደ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ በህግ ዘርፍ ተመርቀው የበቁ፣ የነቁ ባለሞያዎች ሳይቀር እይታቸው በጥያቄዎቹ ተጽዕኖ ስር ሲወድቅ ይስተዋላል፡፡ በተለይ ፍርድ ቤቶች አልተከለከለም/አልተፈቀደም በሚል ዘይቤ እየተመሩ ትዕዛዝ፣ ብይንና ፍርድ የሚሰጡበት አጋጣሚ ትንሽ የሚባል አይደለም፡፡

‘አልተከለከለም/አልተፈቀደም’ መነሻው ከላቲን አባባሎች (Latin Maxims) ሲሆን ሙሉ አገላለጹ በላቲን Tout ce que la loi ne defend pas est permis በእንግሊዝኛ ደግሞ Everything that the law does not forbid is permitted. የሚል ነው፡፡ ወደ አማርኛ ስንመልሰው ‘ህጉ ያልከለከለው ሁሉ የተፈቀደ ነው’ የሚል ይዘት አለው፡፡

ይሄንን ጨምሮ በርካታ የላቲን አባባሎች ለአገራችን የህግ ባለሞያዎች እንግዳ አይደሉም፡፡ በህግ ትምህርት፣ መጣጥፎችና ጥናታዊ ጽሑፎች ላይ የላቲን አባባሎችን መጠቀም ብልህ ባያስብልም ብዙም አያስወቅስም፡፡ በእርግጥ ለማስታወስ ምቹ ከመሆናቸውና እምቅ ሀሳብ በቀላሉ ለማስተላለፍ ካላቸው ሀይል አንጻር በህግ ጽሑፎችና መጻህፍት ላይ እንደ አግባብነቱ ጥቅም ላይ ቢውሉ ፀሐፊን አያስተችም፡፡ ሆኖም ህጉን ለመረዳት ወይም ለማብራራት እንጂ ለመተርጎም ቦታ ሊሰጣቸው አይገባም፡፡ በተለያዩ የህግ ስርዓቶች ያሉ የህግ ምሁራን በላቲን አባባሎች ላይ ፊታቸውን ባያዞሩም ብዙም ለህግ ትርጉም ተጠቃሽ መሆናቸውን ይቃወማሉ፡፡

James Fitzjames Stephen የተባለ አንድ የ19ኛ ክፍለ ዘመን የህግ ምሁር እንዳለው፤

It seems to me that legal maxims in general are little more than pert headings of chapters. They are rather minims than maxims, for they give not a particularly great but a particularly small amount of information. As often as not, the exceptions and disqualifications to them are more important than the so-called rules

የላቲን አባባሎችን እያጣቀሱ ህግ መተርጎም በተለይ በሰበር ችሎት ዘንድ በስፋት ተቀባይነት ያገኘ የአተረጓጎም ስልት ሆኗል፡፡ ጠቅለል ተደርጎ ሲታይ ከህጉ መንፈስና ይዘት ይልቅ በአባባል መመራት ከህግ አውጪው ሀሳብ በግልጽ የማፈንገጥ ያክል ነው፡፡ በውጤቱም ወጥነትንና ተገማችነትን ያዳክማል፡፡

አልተከለከለም/አልተፈቀደም እያሉ ማመዛዘን በከፊልም ቢሆን ተገቢነት የሚኖረው በአንድ ሁኔታ ውስጥ ብቻ ነው፡፡ ይህም ቢሆን አጠቃላይ ስለ ህግ ያለንን ግንዛቤ ከማንፀባረቅ የዘለለ በፍርድ ቤት አከራካሪ የሆነ ጭብጥ ለመፍታት የሚያስችል የአተረጓጎም ስልት አይደለም፡፡ ለግለሰባዊ መብቶች ቅድሚያ በሚሰጡ እንደ እንግሊዝ ባሉ አገራት በመርህ ደረጃ በህግ ክልከላ ያልተደረገባቸው ነገሮች ሁሉ ለዜጋው እንደተፈቀዱ ግምት የሚወሰድበት ሲሆን እንዲህ ዓይነቱ አመለካከት ዜጎች ግልፅ ክልከላ በሌለበት ያለ ስጋትና መሸማቀቅ በነፃነት እንዲኖሩ ያስችላቸዋል፡፡ ከዚህ በተቃራኒ ‘በግልፅ ያልተፈቀደ ሁሉ የተከለከለ ነው’ የሚለው አመላከከት ተፈጻሚነቱ ከመንግስት ስልጣን ጋር በተያያዘ ነው፡፡ ስለሆነም የአስተዳደር አካላት፣ ሹመኖች፣ ባለስልጣናት እና ሌሎች ከህግ የመነጨ ስልጣን የተሰጣቸው ተቋማት በህግ ተለይቶ ከተሰጣቸው ስልጣን ውጪ ማናቸውንም ውሳኔ ሆነ እርምጃ ከመውሰድ እንደተከለከሉ ግምት ይወሰድበታል፡፡ ይህ አመለካከት የመንግስትን ስልጣን ግልፅ በሆነው የህግ ማዕቀፍ ውስጥ ብቻ በመገደብ ለዜጎች መብትና ነፃነት ከለላ ይሰጣል፡፡

ከላይ ከተጠቀሰው ጠቅለል ያለ የህግ አመለካከት ውጪ በፍርድ ቤት በሚካሄድ ሙግት ላይ የስነ-ስርዓት ወይም የስረ-ነገር ህጉን ለመተርምና ተፈጻሚ ለማድረግ አለመከልከል ሆነ አለመፈቀድ አንደኛውን ተከራካሪ ረቺ ሌላኛውን ተረቺ የሚያደርገው አይሆንም፡፡ አልተከለከለም/አልተፈቀደም በህግ አተረጓጎም ውስጥ ሰርጎ ከገባ በአሉታ የማመዛዘን አባዜን ያነግሳል፡፡ ይህ ደግሞ በተራው ዳኞች አንዴ አልተከለከለም አንዴ አልተፈቀደም እያሉ ለውሳኔያቸው ምክንያት በመስጠት ህግን ከመተርጎም ሚናቸው እንዲርቁ ያደርጋቸዋል፡፡ ለዚህ እንደማሳያ በወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ህጉ ይግባኝ ስለሚባልባቸው/ስለማይባልባቸው ጉዳዮች አስመለክቶ በሁለት ሰበር መዝገቦች የተሰጡ ውሳኔዎችን እናያለን፡፡

በወንጀል ጉዳይ የትዕዛዛ ይግባኝ ስላለመኖሩ በወ/መ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 184 ተደንግጓል፡፡ ይግባኝ የማይባልባቸው ትዕዛዞች በድንጋጌው ስር ተዘርዝረዋል፡፡ በዝርዝሩ ውስጥ ያልተካተተ ጉዳይ ይግባኝ ሊባልበት የሚቻል ስለመሆኑ ለመወሰን አልተፈቀደም/አልተከለከለም በማለት በአሉታ በማመዛዘን ፍሬያማ ውጤት ላይ አንደርስም፡፡ ምክንያቱም አልተከለከለም የሚለውን አባባል ከተከተልን በወ/መ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 184 ስር ያልተዘረዘሩ በርካታ ትዕዛዞች ዋናው ክርክር ከመቋጨቱ በፊት ለይግባኝ ምክንያት ስለሚሆኑ ፍትሕ መፋጠኑ ይቀርና ይንዛዛል፡፡ በተቃራኒው አልተፈቀደም የሚለው አሉታዊ የማመዛዘን ዘይቤ የምንከተል ከሆነ መሰረታዊና ህግ መንግስታዊ መብቶችን በሚመለከቱ ጉዳዮች ሳይቀር ይግባኝ ስለሚከለከል ፍትሕ ይዛባል፡፡ ሆኖም በአሉታ የማመዛዘን አባዜ የሚያስከትለው ችግር ከፍትሕ መንዛዛትና መጓደል የዘለለ ነው፡፡ ከላይ ለመጠቆም እንደተሞከረው በአሉታ የማመዛዘን አባዜ ሲነግስ ፍርድ ቤቶች አልተከለከለም አሊያም አልተፈቀደም በማለት እያማረጡ ውሳኔ ለመስጠት ሰፊ ስልጣን ስለሚኖራቸው ከትክክለኛው ህግን የመተርጎም ሚናቸው እንዲሸሹ ያደርጋቸዋል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 93234 ቅጽ 17[1] /አልተከለከለም/

በዚህ መዝገብ ዓቃቤ ህግ በሚያቀርበው የክስ ማሻሻል ጥያቄ ይግባኝ እንዳልተከለከለ አቋም ተይዞበታል፡፡ ለዚህ አቋም እንደ ማሳመኛ የተጠቀሰው ምክንያት ህጉ ያልከለከለው መሆኑ ብቻ ነው፡፡ ሐተታው እንደሚከተለው ይነበባል፡፡

ተከሳሹን ጥፋተኛ በማለት ወይም ነፃ በመልቀቅ ወይም ለጊዜው በመልቀቅ ውሳኔ ከተሰጠ በኃላ በዋናው ጉዳይ በተሰጠው ውሳኔ ላይ ከሚቀርበው ይግባኝ ጋር በአንድነት ካልሆነ በቀር በቁጥር 94 መሰረት ቀጠሮ መስጠትን ወይም አለመስጠትን ወይም በቁጥር 131 መሰረት የሚቀርብ መቃወሚያን ወይም በቁጥር 146 መሰረት ማስረጃን መቀበልን ወይም አለመቀበልን አስመልክቶ በሚሰጡ ትዕዛዞች ላይ ይግባኙን ነጥሎ ማቅረብን የሚከለክል ነው፡፡

እንደሚታየው ይህ ድንጋጌ ትዕዛዞቹ መሰረት የሚያደርጓቸውን ድንጋጌዎች ጭምር በመጥቀስ ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊት የትዕዛዝ ይግባኝ ክልከላ የተጣለባቸውን ጉዳዮች የሚዘረዝር ሲሆን ከዝርዝሩ ውስጥ የክስ ማሻሻል ጉዳይም ሆነ የክስ ማሻሻል ጉዳይ መሰረት የሚያደርጋቸውን ቁጥር 118 እና 119 ድንጋጌዎች አልተካተቱም፡፡ ይህም ሕጉ የትዕዛዝ ይግባኝ ክልከላ በግልጽ ከጣለባቸው ውጪ በሆኑ የመጨረሻ ትዕዛዝ በተሰጠባቸው ጉዳዮች ላይ (የክስ ማሻሻል ጥያቄን አልተካተቱም፡፡ ይህም ሕጉ የትዕዛዝ ይግባኝ ክልከላ በግልጽ ከጣለባቸው ውጪ በሆኑ የመጨረሻ ትዕዛዝ በተሰጠባቸው ጉዳዮች ላይ (የክስ ማሻሻል ጥያቄን ውድቅ ከማድረግ ጉዳይ ጋር የተያያዙትን ጨምሮ) ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊትም ቢሆን ይግባኝ ማቅረብን አስመልክቶ የስነ ስርዓት ሕጉ ያስቀመጠው ክልከላ አለመኖሩን መገንዘብ የሚያስችል ነው፡፡ (ሰረዝ የተጨመረ)

ሰ/መ/ቁ 74041 ቅጽ 13[2] /አልተፈቀደም/

ሆኖም የሰበር ችሎት ከወ/መ/ስ/ስ/ህ/ቁ 184 እና 185 ጣምራ ንባብ በመነሳት ህጉን እንደተረጎመው ተከሳሽ እንዲከላከል በተሰጠበት ትዕዛዝ ላይ ይግባኝ ማቅረብ አይችልም፡፡ እንደዛም ሆኖ በትዕዛዙ ላይ ይግባኝ ቀርቦ ከፀና ጉዳዩ ከመነሻው ይግባኝ እንዲባልበት በህግ ስላልተፈቀደ በማጽናት የተሰጠው ውሳኔ እንደ መጨረሻ ፍርድ ተቆጥሮ ለሰበር ለመቅረብ ብቁ አይደለም፡፡ በዚህ ነጥብ ላይ የሰፈረው አስተያየት እንደሚከተለው ይነበባል፡፡

የተሻሻለው የፀረ ሙስና ልዩ የሥነሥርዓት እና የማስረጃ ህግ አዋጅ ቁጥር 434/1997 አዋጅ አንድ ሰው በሙስና ወንጀል ተከሶ የኮሚሽኑ አቃቤ ሔግ ማስረጃ እንደክሱ ያስረዳ ስለመሆኑ ፍ/ቤቱ አምኖ የመከላከያ ማስረጃ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ቢሰጥ በዚህ ትዕዛዝ ላይ ይግባኝ ለማቅረብ የሚቻል ስለመሆኑ በግልጽ ያስቀመጠው ድንጋጌ የለም፡፡ (ሰረዝ የተጨመረ)

በወንጀለኛ መቅጫ ሕግ አንቀጽ 184 እና 185 ስር የተመለከቱት ድንጋጌዎች አንድ ተከሳሽ የመከላከያ ማስረጃ እንዲያቀርብ ፍ/ቤቱ በወ/መ/ሕ/ሥ/ሥ/ቁጥር 142(1) መሰረት ብይን ሲሰጥ ይግባኝ ለማቅረብ የሚቻል መሆኑን አያሳዩም፡፡ (ሰረዝ የተጨመረ)

[1] አመልካች የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ዐቃቤ ሕግ እና ተጠሪ አቶ ኃይለኪሮስ ወልደብርሃን ካሕሳይ መስከረም 27 ቀን 2007 ዓ.ም.

[2] አመልካች እነ አንተነህ መኮንን እና ተጠሪ የፌደራል ስነ-ነግባርና ጸረ-ሙስና ኮሚሽን ዓቃቤ ህግ ሰኔ 4 ቀን 2004 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

ተቃርኖ ንባብ

$
0
0

እጅግ በርካታ በሆኑ የሰበር ውሳኔዎች የህግ ትርጉም ለማበጀት ተመራጭ ሆኖ የተወሰደው የአተረጓጎም ስልት ሁለት እና ከዚያ በላይ ድንጋጌዎችን በማነጻጸር ቅራኔያቸውን መፍታት ነው፡፡ ይህ የህግ አተረጓጎም ዘዴ ልዩ ሕግ ከአጠቃላይ ሕግ ቅድሚያ ይሰጠዋል (The special prevails over the general) እየተባለ የሚጠራው ሲሆን ተፈጻሚ ሲደረግ በጠቅላላ ህግ የሚገኘው ድንጋጌ ተትቶ በተቃራኒው በልዩ ህግ ያለው ድንጋጌ ውጤት ይሰጠዋል፡፡ በዚህ መልኩ ህጉን መተርጎም ትክክል ቢሆንም የትክክለኛነቱ መሰረት የተቃርኖ መኖር ነው፡፡ የሚነጻጸሩት ድንጋጌዎች በውስጣቸው ሊታረቅ የማይችል ተቃርኖ እንዳላቸው ሳይረጋገጥ ልዩ ህግ ከአጠቃላዩ ህግ ቅድሚያ ሊሰጠው አይገባም፡፡

ይህ በብዙ የሰበር ውሳኔዎች ላይ የሚንጸባረቅ መሰረታዊ ችግር ነው፡፡ ማዛመድና ማቃረን ከሌለ ህግ መተርጎም የማይቻል ነው የሚመስለው፡፡ አርፈው በሰላም የተቀመጡ፣ ሊጋጩ ቀርቶ የማይነካኩ፣ እርስ በእርስ የማይደራረሱ አንቀጾች በግድ እንዲቃረኑ ይደረጋል፡፡ ከዚያም ለልዩ ህግ ዕውቅና በመስጠት የማስታረቅ ስራ ይሰራል፡፡ ሆኖም ተቃርኖ በሌለበት ልዩ ሕግ ከአጠቃላይ ሕግ ቅድሚያ ይሰጠዋል (The special prevails over the general) የሚለው መርህ ሁለት ያልተጣሉ ሰዎችን ለማስታረቅ የመዳከር ያክል ትርጉም የሌለው ህግ የመተርጎም ስራ ነው፡፡

በአስረጂነት በአንድ መዝገብ ላይ በሰበር ችሎት የተሰጠውን የህግ ትርጉም እና አተረጓጎም እናያለን፡፡

በሰ/መ/ቁ. 24703 ቅጽ 7[1] የመድን ገቢው ፊርማ ሳይኖር በአንድ ወገን በመድን ሰጪው ብቻ የተፈረመ የመድን ውል በስር ፍርድ ቤት ዋጋ በማጣቱ ችሎቱ ይህን ስህተት ለማቃናት የፍ/ብ/ሕ/ሥ/ቁ.1725 እና 1727 ድንጋጌዎችን ከን/ህ/ቁ. 657 ጋር በማነጻጸር የተገኘውን ‘ተቃርኖ’ ልዩ ህግ የሆነውን የኋለኛውን ድንጋጌ ተፈጻሚ በማድረግ ‘ለማስታረቅ’ ችሏል፡፡ በዚህ ነጥብ ላይ በችሎቱ በተደረሰበት መደምደሚያ፤

በእርግጥ በፍ/ብሄር ሕጉ በተለየ የአጻጻፍ ሥርአት መደረግ ከሚገባቸው ውሎች መካከል አንዱ የኢንሹራንስ ውል ሲሆን የዚህ ዓይነት ውሎችም በተዋዋይ ወገኖች መፈረም እንዳለባቸውና በሁለት ምስክር ፊትም መረጋገጥ እንዳለባቸው በፍ/ብ/ሕ/ቁ. 1725 እና 1727 ላይ የተመለከተ ቢሆንም የግራ ቀኙን ግንኙነት በተለይ የሚገዛው ልዩ ሕግ የሆነው የንግድ ሕጉ ስለሆነና በጠቅላላ ሕግና በልዩ ሕግ መካከል አለመጣጣም በሚኖርበት ጊዜ ልዩ ሕግ የበላይነት እንደሚኖረው /The special prevails over the general/ ከሕግ አተረጓጐም መርህ መገንዘብ የሚቻል እንደመሆኑ በዚሁ መሰረትም መድን ሰጪው በሚያዘጋጀው ፖሊሲ ላይ መድን ሰጭው መፈረም እንዳለበት በን/ህ/ቁ. 657 ከመመልከቱ በስተቀር መድን ገቢው መፈረም እንደሚገባው ያልተመለከተ በመሆኑ በውል ማቅረቢያ /offer/ ሰነዱ ላይ መድን ገቢው ከፈረመና በፖሊሲው ላይ ደግሞ መድን ሰጭው ከፈረመ በሁለቱ መካከል የመድን ውል ስለመደረጉ በቂ አስረጂ እንደሆነ ከንግድ ህጉ አኳያ መገንዘብ ይቻላል፡፡

ከላይ በተጠቀሰው መዝገቦች ችሎቱ የተጠቀመው የህግ አተረጓጎም ስልት እና መጨረሻ የደረሰበት ግኝት (የህግ ትርጉም) ሙሉ በሙሉ ያረፈው በተነጻጸሩት ድንጋጌዎች መካከል ስለመኖሩ ግምት የተወሰደበት ተቃርኖ ነው፡፡ ሆኖም ከችሎቱ ግምት በስተቀር በተጨባጭ ተቃርኖ ስለመከሰቱ አሳማኝ ምክንያት አልቀረበም፡፡ ሊቀርብም አይችልም፡፡ ምክንያቱም በተጠቀሱት ድንጋጌዎች ስምምነት እንጂ ተቃርኖ የለም፡፡ በን/ህ/ቁ. 657 ላይ መድን ገቢው መፈረም እንደሚገባው አለመመልከቱ በጠቅላላ የውል ህግ ድንጋጌዎች (ፍ/ብ/ሕ/ቁ. 1725 እና 1727) ሊደፈን የሚገባው ክፍተት ነው፡፡ ክፍተት ከተቃርኖ ይለያል፡፡ ለምሳሌ በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ቁ. 377/96 ስለ ተዋዋይ ወገኖች ችሎታ አለመመልከቱ ከጠቅላላ የውል ህግ ድንጋጌዎች ጋር አይቃረንም፡፡ ይልቅስ ይጣጣማል፡፡ የጠቅላላ ድንጋጌዎች ዓይነተኛ ፋይዳም ይኸው ነው፤ በሁሉም ልዩ ውሎች ላይ ተፈጻሚነት ያላቸውን የጋራ ደንቦች መወሰን፡፡

የልዩ ህግ የአተረጓጎም መርህ ቁልፍና ቀዳሚ ሁኔታ ከመነሻው ተቃርኖ ስለመኖሩ በጥልቀትና በጥንቃቄ ማጣራት ነው፡፡ ቁም ነገሩ ያለው የሚጣጣመውን ከሚቃረነው አበጥሮ መለየት መቻሉ ላይ ነው፡፡ ይህ አንኳር ነጥብ ችሎቱ ራሱ በሰ/መ/ቁ/ 21448 ቅጽ 4[2] በቀላል ግን ደግሞ ጥልቅ መልዕክት ባዘለ አገላለጽ እንደሚከተለው አስቀምጦታል፡፡

በተለያዩ የሕጉ ክፍሎች በሚገኙ ድንጋጌዎች መካከል ቅራኔ ከማፈላለግ ይልቅ ተደጋጋፊ ሆነው የጋራ ዓላማ የሚያሳኩበትን የሕግ ትርጉም መሻት የሕግ ባለሙያዎች ሊመርጡት የሚገባ የሕግ አተረጓጎም ዘይቤ ነው፡፡ ስለዚህ ልዩ ሕግ ጠቅላላ ዓላማ ካለው ሕግ ቅድሚያ ይሰጠዋል የሚለውን ዘይቤ ተከትሎ ውሳኔ ላይ ከመድረስ በፊት በእርግጥ የማይታረቅ፣ ምክንያታዊ የሆነ፣ በላቀ የሕግ አውጪው ፍላጐት የተደገፈ ግጭት መኖሩን ማረጋገጥ ያስፈጋል፡፡

ችሎቱ በዚሁ መዝገብ ላይ የተፈጻሚነት ወሰንኑን አስመልክቶ በአጽንኦት እንዳሰመረበት ልዩ ሕግ ከአጠቃላይ ሕግ ቅድሚያ ይሰጠዋል የሚለው የአተረጓጐም ስልት፤

…ተግባራዊ የሚሆነው ሁለት የህግ ድንጋጌዎች የሚጋጩ ሲሆንና ሁለቱም ድንጋጌዎች አንድ ላይ ተግባራዊ ማድረግ ሳይቻል ሲቀር ብቻ ተፈፃሚነት የሚኖረው የአተረጓጐም ዘይቤ በመሆኑ ይህን ዘይቤ ለመምረጥ በቅድሚያ በሁለቱም ሊታረቅ የማይችል ቅራኔ መኖሩን ማረጋገጥ ይጠይቃል፡፡

ይህ መሪ ሀሳብ አከራካሪ ሆኖ ከተነሳው ጉዳይ አንጻር በአንድ በኩል ልዩ የሆነው የሽያጭ ሕግ የሚፀና ውል እንዲኖር የሽያጭ ውል ጽሑፍ ያስፈልጋል ማለቱ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ጠቅላላ ደንቦችን የሚገዛው የውል ሕግ ለሚፀና የማይንቀሳቀስ ንብረት ሽያጭ ውል ከጽሑፍ በተጨማሪ አዋዋይ ፊት መከናወኑ አስፈላጊ መሆኑን ከሚገልፀው ጋር ይጋጫል? ሁለቱንም ማጣጣምስ አይቻልም? የሚለው ጥያቄ ተመርምሯል፡፡ በዚህ ረገድ የተደረሰበት ድምዳሜ የሚከተለው ነው፡፡

የሕጉ አንቀጽ 2877 የሽያጭ ውል በጽሑፍ ካልሆነ በቀር አይፀናም ከማለት ሌላ በአዋዋይ ፊት መከናወን አያስፈልግም የሚል ድንጋጌ የለውም፡፡ በመሆኑም የሽያጭ ሕግ በውልም ሕግ ለተጠቀሰው የጽሑፍ አስፈላጊነት አፅንኦት ከመስጠቱ ሌላ የመረጋገጥን (authentication) አስፈላጊነት አላስቀረም በማለት የሁለቱን ድንጋጌዎች ላይ ላዩን የሚታይ ቅራኔ (apparent contradiction) ማስታረቅ ይቻላል፡፡

የችሎቱ ሀሳብ ቅራኔ አለመኖሩን በድፍረት አያስረግጥም፡፡ ቅራኔ ላይና ታች አያውቅም፡፡ ከላይ ለመጠቆም እንደተሞከረው የጠቅላላ ህግ ፋይዳ ድግግሞሽን በማስቀረት በእያንዳንዱ ልዩ ህግ ላይ የጋራ ተፈጻሚነት ያላቸውን ደንቦች መወሰን ነው፡፡ ስለሆነም የሕጉ አንቀጽ 2877 ከቁጥር 1723 ጋር ቢነጻጸር ‘ላይ ላዩን የሚታይ’ ቅራኔ እንኳ የለውም፡፡ በሰ/መ/ቁ. 24703 የተጠቀሱት ድንጋጌዎች እንዲሁ የሚስማሙ እንጂ የሚጋጩ አይደሉም፡፡ ለመድገም ያክል የማይቃረኑ ድንጋጌዎችን ማስታረቅ ያልተጣሉ ሰዎችን የማስታረቅ ያክል ትርጉም የሌለው የህግ አተረጓጎም ነው፡፡

[1] አመልካች የኢትዮጵያ መድን ድርጅት እና ተጠሪ የቤንሻንጉል ጉሙዝ ብ/ክ/መ/ት ቢሮ ሚያዝያ 9 ቀን 2000 ዓ.ም.

[2] አመልካች ወ/ሮ ጎርፌ ወርቅነህ እና መ/ሰጭዎች እነ ወ/ሮ አበራሽ ደባርጌ ሚያዚያ 30 ቀን 1999 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

የትምህርት ውሎችና የሠራተኛው የማገልገል ግዴታ

$
0
0
ይህ ጽሑፍ የተወሰደው ‘አሠሪና ሠራተኛ ህግ’ ከሚለው በህትመት ላይ ከሚገኝ መጽሐፌ ሲሆን የእንግሊዝኛውን ቅጂ ‘The Duty to serve: Cassation Bench
 on the legal effects of employer-sponsered Tuition Assistance’ በሚል ርዕስ በዚሁ ብሎግ ላይ ታገኙታላችሁ፡፡

‘አሠሪና ሠራተኛ ህግ’ የሚለው መጽሐፍ በተያዘለት የህትመት ሰሌዳ መሰረት ከ20 ቀናት በኋላ ገበያ ላይ ይውላል፡፡ በዚህ አጋጣሚ ከዚህ ቀደም ስለመጽሐፉ በሰጠሁት
መግለጫ መነሻነት በስልክና በኢሜይል ‘መጽሀፉ የት ደረሰ?’ እያላችሁ ላበረታታችሁኝ ውድ የብሎጉ ጎብኚዎች እጅግ የከበረ ምስጋናዬን ልገለፅ እወዳለው፡፡
ስለ መጽሐፉ በተነሳ ቁጥር ስምህን ሳላነሳ የማላልፈው ውድ ወዳጄ ታሪኩ አዱኛ ለህትመቱ እውን መሆን ስላደረግካቸው ነገሮች ሁሉ ምስጋናዬን አቀርባለው፡፡

የትምህርት ውሎችና የሠራተኛው የማገልገል ግዴታ

በአዋጁ ላይ የአሠሪና ሠራተኛ ግዴታዎች መዘርዘራቸው ተጨማሪ ግዴታዎችን በስምምነት የመወሰን ነጻነትን አይገድብም፡፡ ከህግና ከህብረት ስምምነት ጋር እስካልተቃረኑ ድረስ ተጨማሪ ግዴታዎችና ማዕቀቦች በሥራ ውል ወይም በሌላ ተጨማሪ ውል ሊወሰኑ ይችላሉ፡፡ በብዙ አገራት የሥራ ውሉ ጸንቶ ባለበት ጊዜ ሆነ ከተቋረጠ በኋላ ሠራተኛው ከድርጅቱ የንግድ ሥራ ጋር ተመሳሳይነት ባለው ንግድ ውስጥ እንዳይሰማራ ወይም ለሌላ ተወዳዳሪ ድርጅት እንዳይቀጠር አስቀድሞ በውል ማሰር የተለመደ ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ግዴታ የመስራት ነጻነትን የመገደብ ውጤት ስላለው የስምምነቱ ይዘትና የተፈጻሚነት ወሰን የህግ ቁጥጥር ይደረግበታል፡፡[1]

አሁን ላይ ተፈጻሚነታቸው በሥራ መሪዎች ላይ ብቻ ተወስኖ በቀረው የፍትሐብሔር ህግ ላይ በሚገኙት የሥራ ውል ድንጋጌዎች ላይ ከአሠሪው ጋር ‘መወዳደር እንዳይደረግ የሚደረግ የውል ቃል’ በግልጽ ዕውቅና አግኝቶ ህጋዊ ውጤቱና የተፈጻሚነቱ አድማስ ተለይቶ ቢቀመጥም በዚህ ጉዳይ ላይ የአሠሪና ሠራተኛ አዋጁ ዝምታን መርጧል፡፡ በእርግጥ በተግባርም ሲታይ እንዲህ ዓይነት ውሎች ብዙም አልተለመዱም፡፡ ለሰበር ችሎት ቀርበው የህግ ትርጉም የተሰጠባቸው ክርክሮችም የሉም፡፡ ከተጨማሪ ውሎች ከሚመነጩ ግዴታዎች መካከል በሰበር ችሎት የህግ ትርጉም የሚፈልግ ጉዳይ ሆኖ በተደጋጋሚ እየቀረበ ያለው በትምህርትና ስልጠና ውሎች በሠራተኛው ላይ የሚጣለው የማገልገል ግዴታ ነው፡፡ ይህን ግዴታ የሚፈጥሩትና አፈጻጸሙን የሚወስኑት ውሎች በአሠሪና ሠራተኛ አዋጁ ሆነ በሌላ ህግ ቁጥጥር አይደረግባቸውም፡፡ ስለሆነም ጉዳዩ የህጉን ትኩረት የሚሻ እንደመሆኑ በዚህ ረገድ የሰበር ችሎትን አቋም ማስቃኘቱ ተገቢ ይሆናል፡፡

ግልጽ ስምምነት ስለማስፈለጉ

የማገልገል ግዴታ ከሥራ ውል በቀጥታ አይመነጭም፡፡ የትምህርት ወጪ መሸፈኑ ብቻውን የማገልገል ግዴታን አይፈጥርም፡፡ ሠራተኛው በአሠሪው የተሸፈነለትን የትምህርት ወጪ መልሶ ሊከፍል ካልከፈለ ደግሞ ለተወሰነ ጊዜ አሠሪውን ሊያገለግል ግዴታ የሚገባበት ተጨማሪ ውል ያስፈልጋል፡፡ በእንደዚህ ዓይነቱ ውል የአሠሪው ዋነኛ ግዴታ ለትምህርቱ የሚያስፈልጉ ወጪዎችን መሸፈን ነው፡፡ የትምህርት ዕድሉ በአሠሪው በኩል ከተገኘ ወጪው በሶስተኛ ወገን መሸፈኑ ውሉን የጸና ከመሆን አያስቀረውም፡፡ በአመልካች ወ/ሮ ሃርሴማ ሰለሞን እና መልስ ሰጪ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ (ኅዳር 16 ቀን 2001 ዓ.ም. ሰ/መ/ቁ. 33473 ቅጽ 8) መካከል በነበረው ክርክር የኔዘርላንድስ መንግስት በሰጠው ነጻ የትምህርት ዕድል መልስ ሰጭ ዩኒቨርሲቲ ተጠቃሚ እንዲሆን ከትምህርት ሚኒስቴር በተጻፈ ደብዳቤ መነሻነት አመልካች እንዲወዳደሩ ተደርጎ የትምህርት ዕድሉን አግኝተዋል፡፡ አመልካች በዕድሉ ለመጠቀም እንዲችሉ መልስ ሰጭ የዕረፍት ፈቃድ የሰጣቸው ሲሆን የድጋፍ ደብዳቤም ጽፎላቸዋል፡፡

ከፍቃዱና ከደብዳቤው አስቀድሞ አመልካች ትምህርታቸውን አጠናቀው ሲመለሱ ለአራት ዓመታት መልስ ሰጭን ለማገልገል ግዴታ ገብተዋል፡፡ ግዴታቸውን ባይወጡ ደግሞ መልስ ሰጭ ወይም ሶስተኛው ወገን የከፈለላቸውን የትምህርት ወጪ ለመክፈል ተስማምተዋል፡፡ አመልካች በሰበር አቤቱታቸው ላይ “ውሉን ልፈርም የቻልኩት ካልፈረምሽ የዓመት ፈቃድና የድጋፍ ደብዳቤ አይሰጥሽም ስለተባልኩ ነው” በማለት ቢገልጹም የፈቃድ ጉድለት መኖሩን ማስረዳት ባለመቻላቸው ክርክራቸውን ውድቅ ተደርጓል፡፡ በተጨማሪም የትምህርት ዕድሉን የሰጠው አካል ያወጣውን ወጪ ሊከፍሉ እንደማይገባ ያቀረቡት ክርክር በችሎቱ ዘንድ ተቀባይነት አላገኘም፡፡

በሰ/መ/ቁ 40325 (አመልካች የትምህርት ሚኒስቴር እና ተጠሪ ወሰን አሰፋ ሐምሌ 14 ቀን 2001 ዓ.ም. ያልታተመ) ከመደራደር አቅም ልዩነት ጋር ተያይዞ መጎዳትን መሰረት በማድረግ በፍ/ህ/ቁ. 1710(2) ውሉ ውጤት እንዳይሰጠው ጥያቄ ቢቀርብም ችሎቱ አልተቀበለውም፡፡ ተጠሪ በአመልካች የትምህርት ወጪ ተሸፍኖላቸው በሁለት ዓመት ጊዜ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ሲሆን ለእያንዳንዱ የትምህርት ዓመት ሶስት ዓመት በድምሩ ስድስት ዓመት አመልካችን ለማገልገል ግዴታ ገብተዋል፡፡ ውሉን የፈረሙት የመጀመሪያውን የትምህርት ዓመት ካጠናቀቁ በኋ ነው፡፡

ተጠሪ በውላቸው መሰረት ባለመፈጸማቸው ስድስት ዓመት እንዲያገለግሉ ወይም ወጪውን እንዲከፍሉ በአመልካች ክስ ሲቀርብባቸው ውሉ ከጊዜ በኋላ መፈረሙና ለሁለት ዓመት ትምህርት ስድስት ዓመት እንዲያገለግሉ የገቡት ውል ከአመልካች ጋር በነበራቸው የበላይና የበታች ግንኙነት ተገደው የፈረሙት በመሆኑ በፍ/ህ/ቁ. 1710(2) መሰረት ከፍተኛ ጉዳት ስላደረሰባቸው ፈራሽ እንዲባልላቸው ጠይቀዋል፡፡ ጥያቄያቸው ክሱን ባስተናገደው ፍ/ቤት ተቀባይነት አግኝቶ በፍ/ህ/ቁ. 1710(2) አግባብ ፈራሽ ተደርጓል፡፡

ውሳኔው በይግባኝ በመጽናቱ አመልካች የሰበር አቤቱታ ያቀረበ ሲሆን የሰ/ችሎት በተጠሪ የቀረቡትን ምክንያቶች በፍ/ህ/ቁ 1710(2) ከተዘረዘሩት ሁኔታዎች አንጻር በመመርመር ተጠሪ ከአመልካች ጋር ያደረጉት ውል የሚያስከትለውን ህጋዊ ውጤት ለመገንዘብ በቂ የትምህርት ደረጃና እውቀት እንዳላቸው በደረሰበት ድምዳሜ መሰረት ስድስት ዓመት ለማገልገል ግዴታ መግባታቸው አሠሪውን ይጠቅማል ተብሎ ቢወሰድ ውሉ ለአንደኛው ተዋዋይ ወገን የበለጠ ጥቅም መስጠቱ በፍ/ህ/ቁ. 1710(1) የውል ማፍረሻ ምክንያት እንደማይሆን የህግ ትርጉም ሰጥቷል፡፡ እንደ ችሎቱ አስተያየት ተጠሪ ትምህርት ከጀመሩ በኋላ ውሉን እንዲፈርሙ መደረጉ ከፍተኛ ችግር ውስጥ በመሆናቸው ተገደው መፈረማቸውን አያሳይም፡፡

ሠራተኛው ለማገልገል የገባውን ግዴታ ሳይፈጽም ቢቀር ለትምህርቱ የወጣውን ወጪ እንደሚመልስ አማራጭ ግዴታ ሆኖ በውሉ ላይ ይመለከታል፡፡ ሆኖም የማገልገል ግዴታ በግልጽ በውሉ ላይ እስከሰፈረ ድረስ ወጪ የመመለስ ግዴታ በዝምታ ቢታለፍም ከመክፈል ኃላፊነት ነጻ አያደርግም፡፡ አሠሪው በውሉ መሰረት ለትምህርትና ለመሳሰሉት አስፈላጊ የሆኑትን ወጪዎች ከሸፈነ ግዴታውን ተወጥቷል፡፡ የሚቀረው የሠራተኛው የማገልገል ግዴታ ነው፡፡ ግዴታውን ካልፈጸመ በፍ/ህ/ቁ 1771(2) እና 1790(1) መሰረት ኪሳራ የመክፈል ኃላፊነት ይኖርበታል፡፡ (አመልካች የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንቲትዩት እና ተጠሪ አቶ ተፈሪ ማሞ (በሌለበት) ግንቦት 19 ቀን 2002 ዓ.ም. ሰ/መ/ቁ 49453 ቅጽ 10)

አማራጭ ግዴታ

ከላይ በተጠቀሱት የሰበር ውሳኔዎች (ሰ/መ/ቁ 33473 እና 40325) ሆነ በሌሎች ተመሳሳይ መዝገቦች ከማገልገል ግዴታ ጋር በተያያዘ ክስ የሚቀርበው በአማራጭ ዳኝነት በመጠየቅ ነው፡፡ ክስ የሚቀርብለት ፍ/ቤትም ሠራተኛው የማገልገል ግዴታውን በውሉ መሰረት እንዲፈጽም፣ የማይፈጽም ከሆነም ለትምህርት የወጣውን ወጪ እንዲመልስ በአማራጭ ውሳኔ ይሰጣል፡፡ ሠራተኛው ፈቃደኛ ካልሆነ አሠሪውን ለማገልገል አይገደድም፡፡ ተገዶ እንዲፈጽም ማድረግ የግል ነጻነቱን የሚነካ ስለሆነ የፍ/ህ/ቁ 1776 ተፈጻሚነት እንደሌለው በሰ/መ/ቁ 33473 ሆነ በሌሎችም መዝገቦች ወጥና ጽኑ አቋም ተይዞበታል፡፡ ሠራተኛው በገባው ግዴታ መሰረት እንደ ሙያው አሠሪውን ለማገልገል የሚገደደው የፈቀደ እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ለማገልገል ፈቃደኛ ካልሆነ ግን በአማራጭ ለትምህርቱ የወጣውን ወጪ ለመተካት ይገደዳል፡፡

በውል ውስጥ አማራጭ ግዴታ ሲኖር ባለዕዳው በውሉ ከተመለከቱት ሁለት አይነት ግዴታዎች አንዱን መርጦ በመፈጸም ከሁለቱም ግዴታዎቹ ነጻ ይሆናል፡፡[2] ከማገልገል ወይም ወጪ ከመክፈል ግዴታዎች ከሁለቱ አንዱን በመወጣት ውሉን መፈጸም የሚቻል በመሆኑ ከትምህርት ውል የሚመነጭ የማገልገል ግዴታ አማራጭ ግዴታ እንደሆነ እንረዳለን፡፡

ሆኖም ግዴታው ባለመፈጸሙ ክስ ሲቀርብ አማራጭ መሆኑ ይቀራል፡፡ በዚህን ጊዜ ወጪ የመተካት ግዴታ የውሉ አለመፈጸም ውጤት እንጂ በአማራጭ የሚፈጸም ግዴታ አይደለም፡፡ ትምህርቱን አጠናቆ በዛው የቀረ ሠራተኛ ወይም የማገልገል ግዴታውን አቋርጦ ሥራውን የለቀቀ ሠራተኛ በውሉ የተጣለበትን ግዴታ አላከበረም፡፡ ግዴታውን ካላከበረ በሰ/መ/ቁ 49453 እንደተመለከተው በፍ/ህ/ቁ 1771(2) እና 1790(1) መሰረት ኪሳራ ለመክፈል ይገደዳል፡፡

ስለሆነም የማገልገል ግዴታውን አልተወጣም በሚል ክስ ከቀረበበት በአማራጭ ግዴታውን ለመፈጸም የሚያቀርበው ጥያቄ ተቀባይነት አይኖረውም፡፡ በክሱ ላይ በአማራጭ ዳኝነት መጠየቁ ግዴታውን አማራጭ አያደርገውም፡፡ ሲጠቃለል ሠራተኛው በማገልገል ወይም ወጪውን በመክፈል ከሁለቱ በአንዱ በአማራጭ ውሉን የመፈጸም መብት ያለው ቢሆንም አንዴ ግዴታውን አላከበረም ተብሎ ክስ ሲቀርብበት ግን ይህን መብቱን ያጣል፡፡ የማገልገል ግዴታ እያለበት ሥራውን ጥሎ የሄደ ሠራተኛ ክስ ሲቀርብበት “ተመልሼ አገለግላለው” ለማለት አይችልም፡፡ ይህ ሊሆን የሚችለው አሠሪው እስከፈቀደ ድረስ ብቻ ነው፡፡

በዚህ ጉዳይ ላይ የሰበር ችሎት በሰ/መ/ቁ 32769 (አመልካች የኢትዮጵያ አየር መንገድ እና ተጠሪ እነ ሙሉቀን ፍስሐ (2 ሰዎች) ህዳር 9 ቀን 2001 ዓ.ም. ያልታተመ) የሰጠው የህግ ትርጉም ከላይ የተነሳውን ሀሳብ ግልጽ ያደርግልናል፡፡ በዚህ መዝገብ ላይ ሠራተኛው የማገልገል ግዴታውን ባለመወጣቱ አሠሪው ያወጣውን ወጪ እንዲከፍል፣ ዋሱም በዋስትና ግዴታው መሰረት ክፍያ እንዲከፍል በሁለቱም ላይ ክስ የቀረበ ሲሆን ጉዳዩን ያየው ፍ/ቤት ሠራተኛው ለማገልገል ፍቃደኝነቱን ስለገለጸ ክፍያው ሊከፈል እንደማይገባ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ ይግባኙን ያው ፍ/ቤትም ግራ ቀኙን አከራክሮ ውሳኔውን አጽንቷል፡፡ የሰበር ችሎት የስር ፍርድ ቤቶችን ውሳኔ ሲሽር እንዳለው ሠራተኛው፤

“…አገልግሎት መስጠቱን ማቋረጡን ካመነ ሲመቸኝ አገልግሎቱን መስጠት እችላለው በሚል መከራከር አይችልም፡፡”

ግዴታው ተፈጻሚ መሆን የሚጀምርበት ጊዜ

በአንድ የትምህርት መስክ ለመመረቅ የሚፈጀው ጊዜ ውሱን በሆኑ ሁኔታዎች ካልሆነ በስተቀር ትምህርቱ ከመጀመሩ በፊት ይታወቃል፡፡ ይህንን መሰረት በማድረግ በአብዛኛዎቹ የትምህርት ውሎች ላይ ትምህርቱን ለማጠናቀቅ የሚፈጀው ጊዜ ተለይቶ ይቀመጣል፡፡ ትምህርቱ ከተጠናቀቀ በኋላ የማገልገል ግዴታ ተፈጻሚ መሆን ይጀምራል፡፡ ይሁንና በተለያዩ ምክንያቶች የማጠናቀቂያ ጊዜው ሊራዘም ይችላል፡፡

ለምሳሌ ተማሪውን በማይመለከቱ ከአቅም በላይ በሆኑ ምክንያቶች ትምህርቱ በተያዘለት ሰሌዳ የማይጠናቀቅበት አጋጣሚ ይፈጠራል፡፡ ወይም ደግሞ ተማሪውን በሚመለከቱ (ለምሳሌ የጤና ማጣት፣ ዝቅተኛ ውጤት፣ የዲሲፕሊን እርምጃ ወዘተ…) ምክንያቶች ወደ ኋላ መጎተት ይከሰታል፡፡

አንዳንዴ ጊዜ ደግሞ ትምህርቱ ከተጠናቀቀ በኋላ ተጨማሪ ትምህርት የማግኘት ዕድል ይፈጠራል፡፡ በዚህን ጊዜ የማገልገል ግዴታ ተፈጻሚ መሆን የሚጀምረው የመጀመሪያው ትምህርት ሲጠናቀቅ ነው ወይስ ሁለተኛው? የሚል ጥያቄ ይነሳል፡፡ በሰ/መ/ቁ 46574 (አመልካች ሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ እና ተጠሪዎች እነ ዮናስ ካሳ (ሁለት ሰዎች) መጋቢት 3 ቀን 2003 ዓ.ም. ቅጽ 12) የተሰጠው ውሳኔ ለዚህ ጥያቄ ምላሽ ይሰጣል፡፡

በዚህ መዝገብ 1ኛ ተጠሪ ቤልጂየም አገር ሄዶ ለሁለት ዓመት የማስትሬት ትምህርት ሊማርና ትምህርቱን አጠናቆ ሲመለስ ለስድስት ዓመታት አመልካችን ሊያገለግል ግዴታውን የማይፈጽም ከሆነም ለትምህርት የወጡ ወጪዎችን ሊከፍል ከአመልካች ጋር ውል ገብቷል፡፡ 2ኛ ተጠሪም 1ኛ ተጠሪ ግዴታውን ባይወጣ ባልተነጣጠለ ኃላፊነት ወጪውን ለመክፈል ግዴታ ገብታለች፡፡ በዚሁ መሰረት 1ኛ ተጠሪ በአመልካች ድጋፍና ፈቃድ የማስትሬት ትምህርቱን አጠናቋል፡፡ በመቀጠል ተጨማሪ የፒ.ኤች.ዲ የትምህርት ዕድል አሜሪካን አገር በማግኘቱ ትምህርቱን ለመከታተል ሄዷል፡፡

ይህን ተከትሎ አመልካች ለትምህርት የወጣ ወጪ እንዲመለስለት በ1ኛ ተጠሪ እና በዋሱ በ2ኛ ተጠሪ ላይ ክስ አቅርቦ ጉዳዩን ያስተናገደው የሐዋሳ ከተማ ከፍተኛ ፍ/ቤት 1ኛ ተጠሪ በመማር ላይ እንደሆነ በማስረጃ ማረጋገጡን በመጥቀስ 1ኛ ተጠሪ ትምህርቱን ጨርሶ ሲመለስ አመልካች መዝገቡን የማንቀሳቀስ መብቱን ጠብቆ በትዕዛዝ ዘግቶታል፡፡ በትዕዛዙ ላይ የይግባኝ አቤቱታ የቀረበለት የፌ/ከ/ፍ/ቤትም የግራ ቀኙን ክርክር ሰምቶ ትዕዛዙን አጽንቶታል፡፡

የሰ/ችሎት በበኩሉ ክርክሩ ሊወሰን የሚገባው አመልካችና ተጠሪ ያደረጉትን ውል ይዘትና ውሉ ለተዋዋይ ወገኖች የሰጠውን መብትና የጣለውን ግዴታ በመመርመር እንደሆነ በመጠቆም 1ኛ ተጠሪ ግዴታውን ስላለመወጣቱ የሚከተለውን ሐተታ በማስፈር ትዕዛዙን ሽሮታል፡፡

“1ኛ ተጠሪ በውሉ መሠረት ትምህርቱን ጨርሶ የማስተርስ ዲግሪውን ያገኘ ቢሆንም ወደ አገሩ በመመለስ ለአመልካች አገልግሎት አልሰጠም ወይም ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆነም፡፡ ይህም ማለት ውሉ በሰጠው መብት የተጠቀመ (ትምህርቱን የተማረ) ሲሆን፤ ግዴታውን ግን አልፈጸመም፡፡ [የፒ. ኤች ዲ.] ትምህርት እንዲቀጥል የሚያስችለው ተጨማሪ ስምምነትም ከአመልካች አላገኘም፡፡”

የወጪው መጠን

በአብዛኛዎቹ የትምህርት ውሎች ላይ የማገልገል ግዴታን ባለመወጣት ምክንያት ሊከፈል የሚገባው የክፍያ መጠን በቅድሚያ በውሉ ላይ ይገለጻል፡፡ ክስ የሚቀርበውም ሠራተኛው በውሉ ላይ የተመለከተውን ገንዘብ እንዲከፍል ነው፡፡ ሆኖም የሰ/ችሎት በሰ/መ/ቁ 33473 እና 49453 ግልጽ እንዳደረገው ሊከፈል የሚገባው በእርግጥ የወጡ ወጪዎችን እንጂ በውሉ ላይ የሰፈረውን የገንዘብ መጠን አይደለም፡፡ እነዚህም ወጪዎች በቀጥታ ለትምህርትና ተያያዥ ለሆኑ ጉዳዮች (ለምሳሌ ትራንስፖርት፣ መመረቂያ ጽሑፍ ለማዘጋጀት፣ ደመወዝ ወዘተ) የወጡ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ እነዚህ ወጪዎች ስለመውጣታቸው በማስረጃ መረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ በሰ/መ/ቁ 33473 በሶስተኛ ወገን የተከፈሉ በማስረጃ የተረጋገጡ ክፍያዎች ‘በአሠሪው ወጪ’ ውስጥ ተካተዋል፡፡ በዚህ ነጥብ ላይ ችሎቱ በሰጠው አስተያየት ግዴታን ባለመወጣት የሚከፈለው የገንዘብ መጠን በአሠሪው ወይም በሶስተኛ ወገን ለትምህርቱ ሲባል በተጨባጭ የወጣውን ነው፡፡

የማገልገል ግዴታ በከፊል ተፈጽሞ ከሆነ የወጪው መጠን ሲሰላ አገልግሎት የተሰጠበት ጊዜ ከግምት ውስጥ ይገባል፡፡ ስሌቱ ሲሰራ በአገልግሎት ዘመኑ ልክ ወጪውም ተቀናሽ ይደረጋል፡፡ በሰ/መ/ቁ 40325 ተጠሪ ለማገልገል ግዴታ የገቡት ለስድስት ዓመት ሲሆን ትምህርታቸውን ከጨረሱ በኋላ ለአንድ ዓመት አመልካችን አገልግለዋል፡፡ በዚሁ መሰረት እንዲከፍሉ ከተጠየቁት ወጪ ውስጥ አንድ ዓመት ያገለገሉበት ጊዜ ታስቦ ተቀንሶላቸዋል፡፡

የግዴታው አለመፈጸም ተጨማሪ ውጤቶች

የማገልገል ግዴታን አለመፈጸም ለትምህርት የወጣውን ወጪ የመተካት ኃላፊነት ያስከትላል፡፡ ይህ ዋነኛ ውጤቱ ቢሆንም በዚህ ብቻ አይገደብም፡፡ የመጀመሪያው ውጤት ከስንብት ክፍያ ጋር የተያያዘ ሲሆን የማገልገል ግዴታውን ያልተወጣ ሠራተኛ ሥራውን በገዛ ፈቃዱ ሲለቅ የስንብት ክፍያ የማግኘት መብቱን ያጣል፡፡ አምስት ዓመት የአገልግሎት ጊዜ ኖሮት ሥራውን በገዛ ፈቃዱ የሚለቅ ሠራተኛ የስንብት ክፍያ የሚያገኘው ሥራው ላይ የሚያስቆይ ከሥልጠና ጋር የተያያዘ ለአሠሪው የውል ግዴታ[3] የሌለበት እንደሆነ ነው፡፡

በተጨማሪም የማገልገል ግዴታን አለመወጣት የሥራ ውሉ ሲቋረጥ ክሊራንስ የማግኘት መብትን ያሳጣል፡፡ ሆኖም የሥራ ልምድ የምስክር ወረቀት ሊያስከለክል አይገባም፡፡ በሰ/መ/ቁ 48476 (አመልካች የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት እና ተጠሪ አቶ ደረጀ መኮንን ሚያዝያ 12 ቀን 2002 ዓ.ም. ቅጽ 9) ለትምህርት የወጣ ወጪን አለመክፈል በሥራ ልምድ እና ክሊራንስ ላይ ያለውን ህጋዊ ውጤት በተመለከተ የሰ/ችሎት የህግ ትርጉም ሰጥቶበታል፡፡ ክርክሩ የመንግስት ሠራተኞች አዋጅ ቁጥር 515/1999 መሰረት በማድረግ የቀረበ ሲሆን ሠራተኛው በሥራ ላይ እያለም ሆነ በማናቸውም ምክንያት የሥራ ውሉ ሲቋረጥ የሥራ ልምድ የምስክር ወረቀት ሊሰጠው እንደሚገባና ዕዳ አለበት በሚል ሆነ በሌላ በማናቸውም ምክንያት ሊከለከል እንደማይገባ በማተት ችሎቱ የጸና አቋሙን አንጸባርቋል፡፡ በሌላ በኩል መልቀቂያ (clearance) ሠራተኛው ዕዳ እንደሌለበት ማረጋገጫ በመሆኑ አሠሪው ከሠራተኛው የሚፈልገው ዕዳ መኖሩን ከገለጸ በዚህ ረገድ ማስረጃ እንዲሰጥ አይገደድም፡፡

አሠሪው ለትምህርት ያወጣውን ወጪ ስልጣን ባለው ፍ/ቤት ክስ አቅርቦ ከመጠየቅ ውጪ ለሠራተኛው መስጠት ያለበትን የሥራ ልምድ የውሉ መያዣ ሊያደርገው እንደማይችል በሰ/መ/ቁ 48476 አቋም የተያዘበት ሲሆን በተመሳሳይ መልኩ በሰ/መ/ቁ 59666 (አመልካች የኦሮሚያ መንገዶች ባለስልጣን እና ተጠሪ አቶ አቡ ጎበና ግንቦት 4 ቀን 2003 ዓ.ም.ቅጽ 11) አሠሪው ለትምህርት አወጣሁት የሚለውን ወጪ በራሱ ቀንሶ የማስቀረት መብት እንደሌለው ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡ አመልካች ከተጠሪ ጋር የነበረው የሥራ ውል ሲቋረጥ ተጠሪ ከሚከፈለው የዓመት እረፍት እና ስንብት ክፍያ ላይ ለተጠሪ ትምህርት ወጪ ሆኗል ያለውን ገንዘብ በራሱ ስልጣን ቀንሶ ያስቀረ ሲሆን ገንዘቡን ለተጠሪ እንዲመልስ የስር ፍርድ ቤቶች በሰጡት ውሳኔ ላይ ያቀረበው የሰበር አቤቱታ ተቀባይነት አላገኘም፡፡ በችሎቱ ውሳኔ ላይ እንደተመለከተው በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ቁ. 377/96 አንቀጽ 59(1) መሰረት ደመወዝ ለመቀነስ በአሠሪው ስልጣን ላይ የተቀመጠው ገደብ በተመሳሳይ ሁኔታ የሥራ ውል ሲቋረጥ በሚከፈሉ ክፍያዎችም ላይ ተፈጻሚነት አለው፡፡

የዋስ ግዴታ

ወጪው በአሠሪው ተሸፍኖለት በምላሹ ለተወሰነ ጊዜ ለማገልገል ግዴታ ለገባ ሠራተኛ ዋስ መሆን በብዙ መልኩ የከበደ ነው፡፡ በተለይ ትምህርቱ ከኢትዮጵያ ውጭ የሚሰጥ ከሆነ በሚፈጠረው የግንኙነት ክፍተት የተነሳ ሠራተኛው ግዴታውን እንዲወጣ በቅርብ ርቀት ሆኖ ለመከታተልና ለመወትወት ያስቸግራል፡፡ ዋሱ በገባው ግዴታ መሰረት እንዲከፍል ሲገደድም በከፈለው ልክ በአሠሪው እግር ተተክቶ የከፈለውን ለማስመለስ ያለው ዕድል ጠባብ ነው፡፡

ግዴታው የሚቆይበት ጊዜ ርዝመት በዋሱ ላይ ተጨማሪ ጫና ይፈጥራል፡፡ ለምሳሌ ሁለት ዓመት ተምሮ ስድስት ዓመት ለማገልገል ግዴታ ለገባ ሠራተኛ ዋስ የሆነ ሰው ከግዴታው ነጸ ለመሆን ስምንት ዓመት መጠበቅ ይኖርበታል፡፡ አገልግሎቱ የሚጠናቀቅበት ጊዜ ከመድረሱ በፊት ዋሱ ሀሳቡን ቀይሮ ከግዴታው ነፃ የሚወጣበት መንገድም የለም፡፡ ዋሱ በፍ/ሕ/ቁ 1925 በተመለከተው መሰረት የዋስትና ግዴታን ማውረድ የሚቻልበት መንገድ ቢኖርም የድንጋጌው ተፈፃሚነት ግን የባለዕዳው ግዴታ ወደፊት ይደርሳል ተብሎ ለሚታሰብ ሁኔታ ሆኖ ዋስትናው ለስንት ጊዜ እንደሚረጋ በዋስትና ስምምነቱ ላይ ሳይወሰን ከቀረ ነው፡፡ የትምህርት ወጪ ለመመለስ ወይም ለተወሰነ ጊዜ ለማገልገል ግዴታ የሚገባበት ውል በፍ/ሕ/ቁ 1925 በተመለከተው መልኩ ወደፊት የሚሆን ግዴታ ወይም በአንድ ዓይነት ሁኔታ የሚመጣ ግዴታ እንዳልሆነ የሰበር ችሎት በሰ/መ/ቁ 49041 (አመልካች የአ/አ ከተማ አስተዳደር ዋና ኦዲተር መ/ቤት እና ተጠሪዎች እና አቶ ኤሣው መዓዛ (3 ሰዎች) ህዳር 2 ቀን 2003 ዓ.ም ቅጽ 12) የህግ ትርጉም ሰጥቷል፡፡ በመሆኑም ዋሱ በቁጥር 1925 (2) መሰረት የዋስትና ግዴታውን ማውረድ የሚችልበት እድል የለውም፡፡

 

[1] ለምሳሌ ቻይና ወደ ገበያ ኢኮኖሚ መሸጋገሯን ተከትሎ ሠራተኛው አሠሪውን እንዳይወዳደር ገደብ ለሚጥሉ ስምምነቶች ዕውቅና የሰጠች ሲሆን በሠራተኛው ላይ የሚያሳደረውን ኢኮሚያዊ አሉታዊ ጫና ለመቀነስ የሚያስችልና ተፈጻሚነቱ ላይ ቁጥጥር የሚያደርግ የህግ ማዕቀፍም ዘርግታለች፡፡ የበለጠ ለመረዳት Ronald C. Brown, Understanding Labor and Employment Law in China (Cambridge, New York: Cambridge University Press, 2010) ገፅ 163-5 ይመለከቷል፡፡

[2] የፍ/ህ/ቁ 1880

[3] የአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ /ማሻሻያ/ አዋጅ ቁጥር 494/1998 አንቀጽ 2(2) ሸ


Filed under: Articles, Case Comment

ስለ ውክልና- የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0

ውክልና

ተወካይ የሆነ ሰው ወካዩ ለሆነው ሌላ ሰው እንደራሴ ሆኖ አንድ ወይም ብዙ ህጋዊ ስራዎች በወካዩ ስም ለማከናወን የሚገባበት ውል

አንድ ተወካይ የውክልና ስራ በሚፈጽምበት ጊዜ የወካዩን ህጋዊ ሁኔታዎችን የመለወጥ ስልጣን ተሰጥቶታል፡፡ ይህም በመሆኑ ተወካዩ ለወካዩ ፍጹም ታማኝ የመሆን እና የወካዩን ጥቅም ሙሉ ለሙሉ የማስጠበቅ ግዴታ ተጥሎበታል፡፡ ስለሆነም ተወካዩ ስራውን በሚያከናውንበት ጊዜ ቅድሚያ ሊሰጥ የሚገባው የወካዩን ጥቅም ብቻ በመሆኑ የጥቅም ግጭት ባለበት ሁኔታ ተወካዩ በስራው አፈጻጸም ጥንቃቄ ሊያደርግ ይገባል፡፡ ምክንያቱም የጥቅም ግጭት በሚፈጠርበት ጊዜ አንድ ተወካይ ከራሱ ጥቅም ይልቅ የወካዩን ጥቅም ሊያስቀድም ይችላል ተብሎ አይታሰብም፡፡ ስለዚህም ተወካዩ የራሱን ጥቅም የሚመለከት ጉዳይ ሲያጋጥመው ሁኔታውን ለወካዩ ሳያሳውቅና ወካዩ ሳይስማማ ስራውን እንዳይፈጽም ይከለከላል፡፡

ስለወኪልነት የተደነገጉትን የፍ/ብሔር ድንጋጌዎች ስንመለከትም ተወካዩ ከወካዩ ጋር በሚኖረው ግንኙነት ጥብቅ የሆነ ቅን ልቦና ሊኖረው እንደሚገባ እና የውክልና ስልጣኑን የሚያስቀሩ ምክንያቶች ለወካዩ ማስታወቅ እንዳለበት፤ ተወካዩ ስራውን የሚፈጽመው በተለይ ለወካዩ ጥቅም ሊሰጥ በሚችል መንገድ ብቻ መሆን እንዳለበት እንዲሁም ተወካዩ በራሱ ስም ከወካዩ ጋር የሚያደርገው ውል ወካዩ ካላጸደቀው በቀር ሊፈርስ እንደሚችል መደንገጋቸው ተወካዩ ለወካዩ ፍጹም ታማኝ መሆን እንዳለበት እና ለወካዩ ጥቅም ብቻ መስራት እንዳለበት፣ የጥቅም ግጭት ባለበት ጊዜ ሁሉ ሁኔታውን ለወካዩ የማሳወቅ ግዴታ እንዳለበት የሚያስገነዝቡ ናቸው፡፡ በመሆኑም አንድ ተወካይ የጥቅም ግጭት ባለበት ጊዜ ለወካዩ ሳያሳውቅ የሚያከናውነውን ስራ ወካዩ ሊቃወመው የሚችል መሆኑን እና በዚህ ሁኔታ የተከናወነው ስራም ወካዩ ካላፀደቀው በቀር ወካዩ ራሱ እንደፈጸመው ሊቆጠር እንደማይገባ ከውክልና ግንኙነት አጠቃላይ ዓላማ እና ከፍ/ብ/ህጉ ድንጋጌዎች መገንዘብ ይቻላል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 14974 ቅጽ 1፣[1]  ሰ/መ/ቁ. 50440 ቅጽ 10፣[2] ሰ/መ/ቁ. 67376 ቅጽ 13፣[3] ፍ/ህ/ቁ 2198፣ 2208፣ 2209(1)፣ 2188

የአፃፃፍ ስርዓት

የውሉ አጻጻፍ በተለየ ቅርፅ እንዲደረግ ሕጉ የማያስገደድ ከሆነ ይህን ውል እንዲፈጽም በቃል የሚሰጥ የውክልና ስልጣን በወካዩ ላይ ሕጋዊ አስገዳጅነት አለው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 68498 ቅጽ 13፣[4] ፍ/ህ/ቁ. 2180

የወካይ መሞት

በወካይ መሞት ምክንያት ቀሪ በሆነ የውክልና ስልጣን ተወካይ ከነበረው ሰው ጋር በወካዩ ስም የሚደረግ ውል ከጅምሩ ፈራሽና ህጋዊ ውጤት የሌለው ነው፡፡

ወካዩ የሞተ እንደሆነ፣ በሥፍራው አለመኖሩ የተረጋገጠ እንደሆነ፣ ለመስራት ችሎታ ያጣ እንደሆነ ወይም በንግድ መውደቅ ኪሣራ ደርሶበት እንደሆነ ለጉዳዩ ተቃራኒ የሚሆን ውል ካልተገኘ በቀር የውክልና ሥልጣኑ ወዲያውኑ የሚቀር መሆኑን የፍታብሓር ሕ/ቁጥር 2232 ንዑስ አንቀጽ 1 ይደነግጋል፡፡

የውክልና ስልጣን መሻር ውጤት

እንደራሴው ቀሪ በሆነው ሥልጣን መሠረት በሌላ ሰው ስም ወይም ወካይ በነበረው ሰው ስም በሠራ ጊዜ በስሙ የተሠራበት ስው እንደፈቃዱ በስሙ የተሠራውን ሥራ ለማጽደቅ፣ ለመቀበል ወይም ለመሻር መብት አለው፡፡ በማለት በፍ/ብ/ሕ/ቁ. 2191/2/ ከተደነገገ በኋላ በዚሁ በተሰጠው መብት ተጠቅሞ አንዱን መንገድ እንዲከተል ወይም እንዲመርጥ ከእንደራሴው ጋር የተዋዋሉት ሦስተኛ ወገኖች ለማስገደድ እንደሚችሉ እና ሿሚው ከሦስተኛ ወገኖች በቀረበለት ጥያቄ መሠረት ወዲያውኑ ካላስታወቃቸው እንደራሴው የሠራውን ሥራ እንዳልተቀበለው ሕጉ ግምት የወሰደ ለመሆኑ ተከታይ በሆነው ድንጋጌ ተመልክቷል፡፡ እንግዲህ ሿሚው በግልጽም ይሁን በዝምታ እንደራሴው ሥልጣኑ ቀሪ ከሆነ በኋላ የሠራውን ሥራ ያልተቀበለው መሆኑ ከተረጋገጠ የዚሁ ያለመቀበል ውጤት በቁጥር 2193 ተደንግጓል፡፡

የዚህን ድንጋጌ ይዘት ስንመለከት ሿሚው ይህንኑ የእንደራሴውን ሥራ ካልተቀበለው ምን ጊዜም ይኸው ውል ፈራሽ ነው የሚል አይደለም፡፡ ይልቁንም ከፍ/ብ/ሕ/ቁ. 1808 እስከ 1818 ድረስ የተመለከቱትን ድንጋጌዎች ተከትሎ የውሉ መፍረስ ወይም መሰረዝ ሊወሰን የሚችል መሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ይህም እነዚህኑ አግባብነት ያላቸውን ድንጋጌዎች በመከተል ውሉ ሊፈርስ የማይችልበት አጋጣሚ ያለ መሆኑን የሚያሳይና ነገር ግን ውሉ የሚፈርስ ሆኖ በተገኘ ጊዜ ውሉ በመፍረሱ ምክንያት በቅን ልቦና ከእንደራሴው ጋር በተዋዋሉት 3ኛ ወገኖች ላይ ለሚደርሰው ጉዳት ካሣ የሚጠየቅበት መንገድ የሚያመቻች ድንጋጌ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 26399 ቅጽ 5፣[5] ፍ/ህ/ቁ. 1808—1818፣ 2191(2)፣ 2193

ስለማፅደቅ

የውክልና ስልጣን አገልግሎት ውክልናው ከተሰጠበት ጊዜ ጀምሮ ለሚከናወኑ ሕጋዊ ተግባራት እንጂ ከመሰጠቱ በፊት ተወካዩ ለፈጸማቸውን ተግባራት ሕጋዊ ውጤት አይፈጥርም፡፡

ዘግይቶ የተሰጠ የውክልና ስልጣን ተወካዩ የፈጸማቸውን ተግባራት የማጽደቅ ውጤት የለውም፡፡ ምክንያቱም አግባብነት ያላቸው የፍ/ህ/ቁ. 2190 እና ተከታይ ድንጋጌዎች ተፈጻሚ ሊሆኑ የሚችሉት የውክልና ስልጣን ኖሮ ተወካዩ ከውክልና ስልጣኑ በላይ አሳልፎ ለፈጸማቸው ተግባሮች እንጂ ፈጽሞ የውክልና ስልጣን በሌለበት በወካዩ ለተከናወኑ ተግባራት አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 74538 ቅጽ 13፣[6] ፍ/ህ/ቁ. 2190

ልዩ የውክልና ስልጣን

የአንድ ንብረት ባለሃብትነት በውል ለሌላ ሰው የሚተላለፈው ባለሃብት ወይም ባለሃብቱ የንብረቱን ባለቤትነት በውል ለሌላ እንዲያስተላልፍ የፀና ልዩ የውክልና ስልጣን ባለው ሰው እንደሆነ የህገ መንግስቱ አንቀጽ 40 ንዑስ አንቀጽ 1፣ የፍትሐብሓር ህግ ቁጥር 1204 ንዐስ አንቀጽ 2፣ የፍታብሓር ህግ ቁጥር 2005 ንዐስ አንቀጽ 2 እና የፍትሐብሓር ህግ ቁጥር 2232 ንዐስ አንቀጽ 1 ድንጋጌዎችን በጣምራ በማንበብ ለመረዳት ይቻላል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 73291 ቅጽ 13፣ ኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ህገ መንግስት አንቀጽ 40(1)፣ ፍ/ብ/ህ/ቁ. 1204፣ 2232(2)፣ 2015(ሀ)፣ 2005(2)

የማይንቀሳቀስ ንብረት የመሸጥ፣ የመለወጥና የንብረቱን ባለቤትነት ለሦስተኛ ወገን የማስተላለፍ ስልጣን ያለው ተወካይ ንብረት በመያዣ አስያዞ በወካዩ ስም ከባንክ የመበደር ስልጣን አለው፡፡

የውክልና ማስረጃ ለተወካዩ ልዩ የውክልና ስልጣን የሚሰጥ ከሆነ ሕጋዊ ውጤቱ በውክልና ማስረጃው ላይ ከተጻፉት ተግባራት በተጨማሪ በውክልና ማስረጃው የተገለፁትን ጉዳዮችና እንደ ጉዳዩ ክብደትና እንደ ልምድ አሰራር በውክልና ማስረጃው የተገለጹትን ጉዳዮች ተከታታይና ተመሣሣይ የሆኑ አስፈላጊ ተግባራትን የመፈፀም ስልጣንን የሚያካትት መሆኑ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2206 ንዑስ አንቀጽ 1 ይደነግጋል፡፡

በመሆኑም በውክልና ማስረጃ ቤት የመሸጥ፣ የመለወጥና ለሦስተኛ ወገን የማስተላለፍ ስልጣን ያለው ሰው ከዚህ መለስ የሆኑ ተግባራትን የመፈፀም ችሎታ እንዳለውና በተለይም ንብረቱን በመያዣነት ለማስያዝ የሚያስችል ስልጣን እና ችሎታ እንዳለው “ለራሱ ዕዳ ዋስትና እንዲሆን አንዱን የማይንቀሣቀሥ ንብረትን በእዳ መያዣነት አድርጎ ለመስጠት የሚችለው የማይንቀሣቀሰውን ንብረት ለመሸጥ ችሎታ ያለው ሰው ነው” ከሚለው በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 3049 ንዑስ አንቀጽ 2 ድንጋጌ ለመረዳት ይቻላል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 17320 ቅጽ 5፣[7] ፍ/ህ/ቁ. 2026/1/፣ 3049/2/

ተወካዩ ከአስተዳደር ሥራ በቀር ሌላ ሥራ ለመስራት የሚያስፈልግ ሲሆን ልዩ ውክልና እንዲኖረው አስፈላጊ መሆኑንና ተወካዩ ልዩ የውክልና ሥልጣን ከሌለው በቀር የማይንቀሳቀሱ ንብረቶችን ለመሸጥ ወይም አስይዞ ለመበደር የማይችል መሆኑ በፍታብሔር ህግ ቁጥር 2205 ንዑስ አንቀፅ 1 እና ንዑስ አንቀፅ 2 ተደንግጓል፡፡

በወካዩ ስም ማናቸውንም ፎርማሊቲ እያሟላ ንብረት እንዲያዛውር፣ በስሙ እንዲዋዋል የውክልና ስልጣን የተሰጠው ተወካይ በወካዩ ስም የሚገኝ የማይንቀሳቀስ ንብረት የመሸጥ፣ የመለወጥ ስልጣን የለውም፡፡

በፍትሐብሔር ህግ ቁጥር 2205 መሠረት የሚሰጥ ልዩ ውክልና በይዘቱ በልዩ ውክልና የሚፈፀሙ እያንዳንዳቸውን ተግባሮች በግልፅ የሚያመለክት መሆን ይገባዋል፡፡

የውክልና ስልጣን የሚተረጎመው ሳይስፋፋ በጠባቡ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 50985 ቅጽ 13፣[8] ፍ/ህ/ቁ. 2204፣ 2205፣ 2181/3/

የውክልና ሰነዱ ይዘት በግልፅ ውክልና ተቀባዩ የተሰጠው ስልጣን የማይንቀሳቀስ ንብረት ለመሸጥ የሚያስችል ስለመሆኑ እየገለፀ ስለልዩ ውክልና አስፈላጊነት የተቀመጠው የፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 2205 በውክልና ስልጣን ሰነዱ ያለመጠቀሱ ውክልናው ልዩ የውክልና ስልጣን አይደለም ብሎ ለመደምደም የሚያስችል ስለመሆኑ የሚያሳይ የሕግ ድንጋጌ የለም፡፡ ዋናውና ቁልፉ ነገር ለውክልና ተቀባዩ የተሰጡት ተግባሮች በዝርዝርና ግልጽ ሁኔታ ተጠቅሰው በውክልና ሰነዱ ላይ መገኘት እንጂ አግባብነት ያላቸው ድንጋጌዎች ያለመጠቀሳቸው አይደለም፡፡ የሰነዱ ይዘት ግልጽ መሆኑ በተረጋገጠበት ሁኔታ አግባብነት ያላቸው ድንጋጌዎች በውክልና ስልጣን ሰጪውና በውክልና ስልጣን ተቀባዩ አልተጠቀሱም ተብሎ ሰነዱ ዋጋ እንዲያጣ ማድረግ የተዋዋዮችን ሐሳብ ውጤት እንዳይኖረው የሚያደርግ በመሆኑ በውል አተረጓጎም ደንቦችም ተቀባይነት የሌለው አካሄድ ነው የሚሆነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 72337 ቅጽ 13፣[9] ፍ/ህ/ቁ. 2199፣ 2055

 

[1] አመልካች ወ/ት ማህሌት ገ/ስላሴ እና ተጠሪ እነ አቶ መንግሥቱ ኃብ /2 ሰዎች/ ሐምሌ 28 ቀን 1997 ዓ.ም.

[2] አመልካች አቶ ሃብቱ ወልዱ እና እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ መሰሉ ደስታ/ 2 ሰዎች/ ግንቦት 16 ቀን 2002 ዓ.ም.

[3] አመልካቾች እነ ወ/ሮ ንግስት ኪዲኔ /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ እነ አቶ በለጠ ወልደሰማያት /2 ሰዎች/ ሀምሌ 30 ቀን 2004 ዓ.ም.

[4] አመልካች አቶ ገብረ ክርስቶስ ገብረ እግዛብሔር እና ተጠሪ ሳባ እምነበረድ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ሰኔ 07 ቀን 2004 ዓ.ም.

[5] አመልካች አቶ ኃ/ማርያም ባዩ እና ተጠሪ እነ አቶ ሳሙኤል ጎሳዬ /5 ሰዎች/ ኅዳር 5 ቀን 2000 ዓ.ም.

[6] አመልካች ወ/ሪት አሊያት ይማም ሙዘይን እና መልስ ሰጭ አቶ እምነቴ እንደሻው ሐምላ 20 ቀን 2004 ዓ.ም.

[7] አመልካች የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ተጠሪ እነ ዶ/ር ሻውል ገብሬ /2 ሰዎች/ መጋቢት 18 ቀን 2000 ዓ.ም.

[8] አመልካች እነ አቶ ስሻህ ክፍሌ /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ አፀደ ደቤ /2 ሰዎች/ ሕዳር 5 ቀን 2004 ዓ.ም.

[9] አመልካች ወ/ሮ ንግስቲ እምነት እና ተጠሪ ቴዎድሮስ ተክሌ የካቲት 26 ቀን 2004 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

የሰበር ውሳኔዎች ግጭት

$
0
0

የሰበር ውሳኔዎች ግጭት

የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከአምስት ያላነሱ ዳኞች በተሰየሙበት የሰበር ችሎት የሚሰጥ የህግ ትርጉም ለበታች የክልልና የፌደራል ፍርድ ቤቶች አስገዳጅነት እንዲኖረው አስገዳጅ ህግ ከወጣ (አዋጅ ቁጥር 454/1997) ከአስር ዓመት ዓመት በላይ አልፎታል፡፡ በእነዚህ ሁሉ ዓመታት ውስጥ ህጉና አፈጻጸሙ ለፍትህ ስርዓቱ ያበረከተው አዎንታዊ አስተዋጽኦ እና ያስከተለው ችግር በተመለከተ የዳሰሳና የክለሳ ጥናት ተደርጎ ውጤቱ ይፋ የሆነ ሪፖርት እስካሁን ድረስ የለም፡፡ እስከ አሁን ድረስ የህጉ አጠቃላይ ተቀባይነት መሰረት ያደረገው አሰራሩ ወጥነትን ያመጣል ከሚል በሀሳብ ደረጃ ሊያሳምን የሚችል አመለካከት እንጂ በተግባር ተፈትኖ እየታየ ያለ ሀቅ አይደለም፡፡

ተግባራዊ የመለኪያ ሚዛንን ለጊዜው ወደ ጎን እንተወውና ወጥነት የአዋጁ ዋና ዓላማና ግብ ነው ብለን እንነሳ፡፡ ችግሩ ግን ከዚህ ይጀምራል፡፡ አዋጅ ቁጥር 454/1997 ወጥነትን እንደ ዋና ሆነ ተጓዳኝ ዓላማና ግብ ይዞ ስለመነሳቱ በግልጽ ሆነ በተዘዋዋሪ የሚናገር ድንጋጌ አልያዘም፡፡

በአዋጁ መግቢያ ላይ እንደተመለከተው የፌደራል ፍርድ ቤቶች አዋጅን እንደገና ለማሻሻል የወጣው አዋጅ ቁጥር 454/1997 ሊወጣ የቻለው ስለፌደራል ፍርድ ቤቶች የወጣውን አዋጅ ቁጥር 25/88 (እንደተሻሻለ) እንደገና ማሻሻል አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ነው፡፡ የአስፈላጊነቱ መሰረት ምን እንደሆነ በግልጽ የተመለከተ ነገር የለም፡፡

አዋጁ ዝምታን ቢመርጥም ህጉ ሊያሳካ የፈለገው ቀዳሚ ግብ የአገሪቱ ፍርድ ቤቶች በተመሳሳይ ጉዳይ የሚሰጧቸው ውሳኔዎች ወጥነት እንዲኖራቸውና ተገማች እንዲሆኑ ለማስቻል እንደሆነ ግምት ቢወሰድ በመርህ ደረጃ አሳማኝና አስማሚ ሀሳብ ነው፡፡ እንግዲህ ወጥነትና ተገማችነት የአገሪቱ የፍትህ ስርዓት ዋነኛው ገጽታ እንዲሆን ከታለመ ከብዙ ነገሮች መሐል ቢያንስ አንድ መሰረታዊ ቅድመ ሁኔታ ተሟልቶ ይገኝ ዘንድ ግድ ይላል፡፡ ይኸውም የሰበር ውሳኔዎች ራሳቸው ወጥነት ዐቢይ መገለጫቸው ሊሆን ይገባል፡፡ ግልጽ የአቋም ለውጥ በሌለበት በተመሳሳይ ጉዳይ ላይ እርስ በእርስ የማይጣጣምና የሚጋጭ የህግ ትርጉም በሚኖርበት ጊዜ በበታች ፍርድ ቤቶች ላይ ውዥንብር በመፍጠር ተገማችነትን አደጋ ውስጥ ይከታል፡፡ አዋጅ ቁጥር 454/1997 ይፋ ህግ ሆኖ ከታወጀ ወዲህ የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሚሰጣቸው ውሳኔዎች ዓመት እየጠበቁ ከመታተማቸው ውጪ በአንድ ጉዳይ ላይ ተፈጻሚ የተደረገውን የህግ ትርጉም በቀላሉ መለየትና ማግኘት የሚያስችል የውሳኔዎች ጥንቅር (Codification) አሁን ድረስ አልተዘጋጀም፡፡ በዚህ የተነሳ በበታች ፍ/ቤቶች ይቅርና በራሱ በችሎቱ ዘንድ እንኳን ወጥነትን ማስፈን አልተቻለም፡፡

እርስ በእርስ ከሚጋጩ የሰበር ውሳኔዎች መካከል ለአብነት ያህል የሚከተሉት በአስረጂነት ይጠቀሳሉ፡፡

  1. ሰ/መ/ቁ 47495 ያልታተመ እና ሰ/መ/ቁ. 47139 ቅጽ 11

በሰ/መ/ቁ 47495 ያልታተመ[1] ችሎቱ ህጉን በመተርጎም በደረሰበት ድምዳሜ መሰረት በሟች ስም ተመዝግቦ የነበረ የውርስ ሀብት በሽያጭ፣ በውርስ፣ በስጦታ ወይም በሌላ ህጋዊ መንገድ መተላለፉ ሳይረጋገጥ ውርሱ በሚጣራበት ጊዜ በአንደኛው ወራሽ ስም ተመዝገቦ እንደሚገኝ ከተረጋገጠ የውርሱ ሀብት ተደርጎ ሊጣራ አይገባውም፡፡ በዚህ ንብረት ላይ መብት አለኝ የሚል ወራሽ የባለቤትነት ምዝገባው ስርዓቱን ጠብቆ ያልተከናወነ ስለመሆኑ ሳያስረዳ እንዲሁም የባለቤትነት ምስክር ወረቀቱን ስልጣን ባለው አካል ሳያሰርዝ ንብረቱን በስሙ ያስመዘገበው ወራሽ እንዴት እንዳፈራው ሊረጋገጥ ይገባል በሚል የሚያነሳው ቅሬታ የሕግ መሰረት ያለው አይደለም፡፡

ሆኖም በሰ/መ/ቁ. 47139 ቅጽ 11[2] የተሰጠው የህግ ትርጉም በግልጽ እንደሚያስገነዝበን አንድ የማይንቀሳቀስ ንብረት በስሙ የተመዘገበ ሰው ንብረቱ በእጁ እንዴት ሊገባ እንደቻለ ማስረዳት ካልቻለ ህጋዊ ወራሽ እንዳያስረክበው ሲጠይቅ የመመለስ ግዴታ አለበት፡፡

  1. ሰ/መ/ቁ 49239 ያልታተመ እና ሰ/መ/ቁ. 114669 ቅጽ 19

በአሠሪና ሠራተኛ ግንኙነት ውስጥ በወንጀል የጥፋተኝነት ፍርድ ሳይኖር አንድ ሠራተኛ ለሰላሳ ወይም ከዚያ በላይ ቀናት ከታሰረ ውጤቱ ምንድነው? ለጥያቄው ምላሽ ከሰ/መ/ቁ 49239 ያልታተመ[3] አንጻር ካየነው ለአምስት ተከታታይ ቀናት ከስራ እንደቀረ ተቆጥሮ የሥራ ውሉ በህጋዊ መንገድ ይቋረጣል፡፡

ይሁን እንጂ በሰ/መ/ቁ. 114669 ቅጽ 19[4] ችሎቱ በሰ/መ/ቁ. 49239 ይዞት የነበረውን አቋም መሻሻሉን በግልጽ ሳይጠቁም የህጉን ትርጉም ቀይሮታል፡፡ በዚህ መዝገብ ተጠሪ የአመልካችን መኪና ሲያሽከረክሩ ግጭት በመከሰቱ ጉዳዩ እስኪጣራ ድረስ ለአራት ወር ከአስር ቀናት በጊዜ ቀጠሮ በእስር ከቆዩ በኋላ ዓቃቤ ህግ የወንጀል ክስ ለመቀጠል የሚያስችል ነገር ባለማግኘቱ መዝገቡን ዘግቶታል፡፡

ተጠሪ ከሰላሳ ቀናት በላይ ከስራ ቀርተዋል በሚል ከስራ ሲሰናበቱ የውሉን መቋረጥ አስመልክቶ ጉዳዩን ያዩት ፍርድ ቤቶች የእስራት ፍርድ ሳይኖር በጊዜ ቀጠሮ መታሰር የሥራ ውል ለማቋረጥ በቂ ምክንያት እንዳልሆነ ወጥ አቋም ላይ ደርሰዋል፡፡ የሰበር ችሎትም ከስር ፍ/ቤቶች አልተለየም፡፡ አከራካሪውን ጭብጥ አስመልክቶ ለህጉ በተሰጠው አስገዳጅ ትርጉም መሰረት፤

“በፍርድ ቤት ውሳኔ ከ30 ቀን በላይ ከስራ [መቅረቱ] ተረጋግጦ ያልተወሰነበት ሰራተኛ ያለማስጠንቀቂያ ከስራ ማሰናበት የአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 27 /1/በ/ ድንጋጌ ይዘትና መንፈስ ያላገናዘበ ነው፡፡”

  1. ሰ/መ/ቁ. 25005 ቅጽ 5 እና ሰ/መ/ቁ. 26839 ቅጽ 5

የማይንቀሳቀስ ንብረት (መኖሪያ ቤት) ግንባታ ከጋብቻ በፊት ቢጀመርም ግንባታው የተጠናቀቀው ባልና ሚስት በጋብቻ ውስጥ በሚኖሩበት ጊዜ ውስጥ ከሆነ በተለይም አንደኛው ወገን ለቤቱ ግንባታ የገንዘብ አስተዋጽኦ አድርጎ ከሆነ በፍቺ ጊዜ ሁለቱም የቤቱን እኩል ድርሻ የማግኘት መብት እንዳላቸው የህግ ትርጉም የተሰጠው በሰ/መ/ቁ. 25005 ቅጽ 5[5] ነው፡፡ ይህ ትርጉም ግን ፀንቶ መቆየት የቻለው ለአንድ ሳምንት ያህል ብቻ ነው፡፡

ኀዳር 10 ቀን 2000 ዓ.ም. በሰ/መ/ቁ. 26839 ቅጽ 5[6] በተመሳሳይ ጉዳይ በተሰጠ የሰበር ውሳኔ መሰረት የማይንቀሳቀስ ንብረት (መኖሪያ ቤት) ግንባታ ከጋብቻ በፊት ተጀምሮ ባልና ሚስቱ በትዳር ውስጥ በነበሩበት ጊዜ ከተጠናቀቀ በፍቺ ወቅት ለንብረቱ መገኘት ተጋቢዎቹ ያደረጉት አስተዋጽኦ ተመርምሮ እንደነገሩ ሁኔታ የግል ወይም የጋራ ሊባል ይገባል፡፡ ይህንንም ለመወሰን በንጽጽር ሲታይ አብዛኛው መዋጮ የተደረገው ከግል ነው ወይስ ከጋራ? የሚለውን ከግምት ማስገባቱ ተገቢ እንደሚሆን በውሳኔው ላይ ተመልክቷል፡፡ የንብረት ክፍፍሉን በተመለከተም ንብረቱ በአብዛኛው ከጋራ ሃብት መዋጮ የተገኘ ከሆነና የግል ንብረቱ ትንሽ ከሆነ ንብረቱ የጋራ ሆኖ እንደሚቆጠር፤ በንብረቱ ላይ የተቀላቀለውን የግል ሃብት በተቀላቀለው መጠን የግሉ የሆነው ተጋቢ ሊወስድ እንደሚገባ ከሰ/መ/ቁ. 25005 ያፈነገጠ አቋም ተይዞበታል፡፡

  1. ሰ/መ/ቁ. 33200 ያልታተመ እና ሰ/መ/ቁ. 44025 ቅጽ 10

በሰ/መ/ቁ. 44025 ቅጽ 10 ንብረት በወራሾች በጋራ ከተያዘ የይርጋ ደንብ ተፈጻሚነትን እንደሚያስቀር ትርጉም ተሰጥቶበታል፡፡ ከአንድ ዓመት በፊት በሰ/መ/ቁ. 33200[7] በተሰጠ ውሳኔ ግን የጋራ ይዞታ ይርጋን ተፈጻሚ ላለማድረግ በምክንያትነት ሊጠቀስ እንደማይገባው ጠንካራ አቋም ተይዞበት ነበር፡፡ በዚህ ነጥብ ላይ የችሎቱ ሐተታ እንደሚከተለው ይነበባል፡፡

ንብረቱ በጋራም ተያዘ በተናጠል የተጠየቀው ዳኝነት የውርስ አጣሪ ተቋቁሞ ንብረት ለመከፋፈል እስከሆነ ድረስ ይሄው ጥያቄያቸው በሕግ በተቀመጠ የጊዜ ገደብ ካልቀረበ በይርጋ የማይታገድበት ምክንያት አይኖርም ጥያቄው ይርጋ የለውም ማለትም የይርጋን ዓላማ ውጤት አልባ ከማድረግ የተለየ አይሆንም፡፡

  1. ሰ/መ/ቁ. 17937 ቅጽ 4 እና ሰ/መ/ቁ. 33200 ያልታተመ

በወራሽና ወራሽ መካከል የሚነሳ የንብረት ማስመለስ ክርክር በ3 ዓመት ይርጋ እንደሚታገድ በሰ/መ/ቁ. 17937 ቅጽ 4[8] እና በቀጣይነት ከተሰጡ በርካታ ውሳኔዎች መረዳት ይቻላል፡፡ ይሁን እንጂ በሰ/መ/ቁ. 33200[9] አንድ በወራሽና ወራሽ መካከል የውርስ ይጣራልኝ አቤቱታ ላይ በሚያቀርበው ክስ ላይ ተፈጻሚነት ያለው ልዩ የይርጋ ድንጋጌ እንደሌለ ተጠቀሶ ይርጋው በፍ/ህ/ቁ. 1845 መሰረት በ10 ዓመት እንደሚታገድ የህግ ትርጉም ተሰጥቷል፡፡

  1. ሰ/መ/ቁ. 32013 ቅጽ 6፣ ሰ/መ/ቁ. 44237 ቅጽ 10 እና ሰ/መ/ቁ. 40418 ቅጽ 10

የውርስ ሃብት ክፍፍል ጥያቄ በፍ/ብ/ሕግ ቁ. 1000/1/ በተመለከተው የሦስት ዓመትም ሆነ በፍ/ብ/ሕግ ቁጥር 974/2/ በተቀመጠው የአምስት ዓመት የጊዜ ገደብ በይርጋ ቀሪ እንደሚሆን በሰ/መ/ቁ. 32013 ቅጽ 6[10] ትርጉም ከተሰጠ ከሁለት ዓመት በኋላ ተመሳሳይ ይዘት ባለው ጉዳይ ግልጽ የአቋም ለውጥ ሳይደረግ የንብረት ክፍፍል ጥያቄ ይርጋ አያግደውም ተብሏል፡፡ በሰ/መ/ቁ. 44237[11] አመልካች የጠየቁት ዳኝነት ወራሽነታቸውን ማረጋገጣቸውንና የውርሱን ሀብት ተጠሪ ይዘው እየተጠቀሙበት በመሆኑ እንዲያካፍሏቸው ቢጠይቋቸው ፍቃደኛ ባለመሆናቸው የውርስ ሀብት አጣሪ በፍርድ ቤት እንዲሾምላቸው ነው፡፡ የሰበር ችሎት አመልካች የጠየቁት ዳኝነት የውርስ ሀብት ክፍፍል እንደሆነ በመጠቆም በፍ/ህ/ቁ. 1062 በማናቸውም ጊዜ ሊቀርብ የሚችልና በይርጋ የማይታገድ እንደሆነ በማተት የፍ/ህ/ቁ. 1000/1/ ድንጋጌን ተፈጻሚ በማድረግ የስር ፍ/ቤቶች ክሱን በይርጋ ውድቅ በማድረግ የሰጡትን ውሳኔ ሽሮታል፡፡

ጥቅምት 10 ቀን 2002 ዓ.ም. በተሰጠ ሌላ ውሳኔ ደግሞ የችሎቱን አቋም ለመጨበጥ አስቸጋሪ አድርጎታል፡፡ ከሰ/መ/ቁ. 40418 ቅጽ 10[12] የህግ ትርጉም መረዳት እንደሚቻለው የውርስ አጣሪው ባቀረበው ሪፖርት መሰረት የቀረበ የንብረት ልካፈል ጥያቄ በፍ/ብ/ሕ/ቁ. 1080/3/ በተደነገገው የአንድ ዓመት የጊዜ ውስጥ ካልቀረበ በይርጋ ይታገዳል፡፡

  1. ሰ/መ/ቁ. 08751 ቅጽ 6 እና ሰ/መ/ቁ. 93137 ቅጽ 15

የክልል ሰበር ሰሚ ችሎት ሐሰተኛ ማስረጃ ላይ ተመስርቶ ውሳኔ ሰጥቷል በሚል የዳግም ዳኝነት ጥያቄ ሊቀርብ የሚገባው ለሰበር ችሎቱ ሳይሆን መጀመሪያ ፍርዱን ለፈረደው የስር ፍ/ቤት ነው፡፡ ይህ በሰ/መ/ቁ. 93137 ቅጽ 15[13] የተያዘው የችሎቱ አቋም በተመሳሳይ ጉዳይ በሰ/መ/ቁ. 08751 ቅጽ 6[14] ከተሰጠው ውሳኔ ጋር አብሮ አይሄድም፡፡ በዚህ መዝገብ ችሎቱ የሰጠው ውሳኔ በተጭበረበረ ሰነድ ላይ በመመስረት እንደሆነ በመግለጽ አመልካች ያቀረቡትን አቤቱታ ተቀብሎ ግራ ቀኙን በማከራከር ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

[1] አመልካች ወ/ሮ ፈለቀች ሽፈራው እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ በቀለች መንግስቱ /2 ሰዎች/ መጋቢት 20 ቀን 2002 ዓ.ም.

[2] አመልካች አቶ የሱፍ ሁሴን እና ተጠሪ አቶ አደን አብደላ ኅዳር 30 ቀን 2003 ዓ.ም.

[3] አመልካች የአ/አ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን እና ተጠሪ አቶ ፍቅሩ ከበደ የካቲት 3 ቀን 2002 ዓ.ም.

[4] አመልካች የኢትዮጵያ መንገዶች ኮንስትራክሽን ኮርፖሬሽን የደብረማርቆስ መንገዶች ጥገና ዲስትሪክት እና አቶ አስማረ ፈጠነ ጥቅምት 24 ቀን 2008 ዓ.ም.

[5] አመልካች መኮንን በላቸው እና ተጠሪ ወ/ሮ አለሚቱ አደም ኀዳር 3 ቀን 2000 ዓ.ም.

[6] አመልካች ወ/ሮ አስካለ ለማ እና ተጠሪ ሣህለ ሚካኤል በዛብህ ኀዳር 10 ቀን 2000 ዓ.ም.

[7] አመልካች አቶ አወል አማን እና ተጠሪዎች እነ አቶ ናሥር አማን /2 ሰዎች/ ያልታተመ ህዳር 11 ቀን 2001 ዓ.ም

[8] አመልካች ወ/ሮ ድንቄ ተድላ እና ተጠሪ እነ አቶ አባተ ጫኔ መጋቢት 20 ቀን 1999 ዓ.ም.

[9] ዝኒ ከማሁ

[10] አመልካች ደምስ ጥበበሥላሴ እና ተጠሪ ቴዎድሮስ ጥበበሥላሴ መጋቢት 25 ቀን 2000 ዓ.ም.

[11] አመልካች ወ/ሮ ሙለሸዋ ቦጋለ – በራሳቸውን እና ወኪል ለሆኑላቸው /4 ሰዎች/ እና ተጠሪ ወ/ሮ ፈልቃ ቤኛ ሰ/መ/ቁ. 44237 ቅጽ 10 መጋቢት 20 ቀን 2002 ዓ.ም.

[12] አመልካች ተስፋዬ ሞላ እና ተጠሪዎች እነ እሸቱ ሞላ /3 ሰዎች/ ጥቅምት 10 ቀን 2002 ዓ.ም.

[13] አመልካች ወ/ሮ ብጥር ታገለ እና ተጠሪ ወ/ሮ አገር ተሰማ የካቲት 11 ቀን 2006 ዓ.ም.

[14] አመልካች ወ/ሮ አበበች በጅጋ እና ተጠሪ እነ ዶ/ር ተስፋዬ አካሉ /2 ሰዎች/ ግንቦት 26 ቀን 2000 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

የመቃወም አቤቱታ—የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0

የመቃወም አቤቱታ —የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

1. ፍርድ መቃወም

ተካፋይ ባልሆነበት ክርክር የተሰጠው ውሳኔ መብቴን ይነካል በማለት አስቀድሞ ለአንድ ወገን የተሰጠውን ውሳኔ ለማሰረዝ በመቃወም አመልካች የሚቀርብ አቤቱታ

የመቃወም አቤቱታ ሲቀርብ ክርክሩ የሚካሄደው በመቃወም አመልካች እና አስቀድሞ በተሰጠው ውሳኔ ተጠቃሚ በሆነው የመቃወም ተጠሪ በሚባለው ወገን መካከል ሲሆን የዚህ ዓይነቱ ክርክር የሚቀርብበት እና የሚመራበት ስርዓት እንዲሁም የዚህ ዓይነቱን ክርክር የሚሰማው ፍርድ ቤት ስላለው ስልጣን በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ ከቁጥር 358 እስከ 360 ተመልክቷል፡፡

የመቃወም አቤቱታው መቅረብ የሚገባው በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 222 እና 223 ድንጋጌዎች መሰረት ክስ እና የማስረጃ መግለጫ የሚቀርብበትን ስርዓት መሰረት በማድረግ ስለመሆኑ በግልጽ ተደንግጎአል፡፡

የመቃወም አቤቱታው እና የማስረጃው ቅጂ የመቃወም ተጠሪ ለሆነው ወገን እንዲደርስ መደረግ የሚገባው መሆኑን ከመግለጽ በስተቀር የመቃወም ተጠሪው የጽሁፍ መልስ እና የመከላከያ ማስረጃ ማቅረብ እንደሚገባው በእነዚህ ድንጋጌዎች ላይ በግልጽ የተጻፈ ባይሆንም የመቃወም ተጠሪ የሆነው ወገን በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 234 ድንጋጌ መሰረት ለቀረበበት የመቃወም አቤቱታ ያለውን የመከላከያ መልስ እና ማስረጃ ማቅረብ የሚገባው ስለመሆኑ ከቁጥር 360(1) እና (2) ድንጋጌዎች ጣምራ ንባብ መገንዘብ ይቻላል፡፡ በተለይም የመቃወሚያው ክርክር የሚሰማው የመጀመሪያው ክርክር በተሠማበት ስነ ስርዓት መሰረት ስለመሆኑ በቁጥር 360(2) የተመለከተው አስገዳጅ ድንጋጌ በቀጥታ የቀረበ ክስ እና ክርክር የሚስተናገድበትን ስርዓት በተመለከተ በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕጉ የተመለከቱት መሰረታዊ ድንጋጌዎች የመቃወሚያ ክርክርን በማስተናገድ ረገድም በተመሳሳይ ሁኔታ ተፈጻሚ ሊደረጉ የሚገባቸው መሆኑን በግልጽ የሚያስገነዝብ ነው፡፡

በዚህ ድንጋጌ የተመለከተው የክርክር አመራር ስርዓት ዓይነተኛ ዓላማ ሁለቱም ተከራካሪ ወገኖች እኩል ዕድል እንዲኖራቸው እና በተለይም የመቃወም አመልካች የሆነው ወገን የክርክሩ ተካፋይ ባልነበረበት ጊዜ የቀረበውን የመቃወም ተጠሪ ወገን የሰው እና የሰነድ ማስረጃ በመስቀልኛ ጥያቄ እና በማስተባበያ ክርክር ጭምር የመፈተን ዕድል እንዲያገኝ ለማስቻል እንደሆነ ይታመናል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 86398 ቅጽ 16፣[1] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 222፣ 223፣ 350-360

የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 358 አንድ የክርክሩ ተካፋይ መሆን የሚገባው ሰው የክርክሩ ተካፋይ ሳይሆን ውሳኔ ተሰጥቶ ከሆነ እና ውሳኔውም ያረፈው በአንድ የክርክሩ ምክንያት በሆነ ንብረት ላይ ሁኖ ይህንኑ የክርክሩ ተካፋይ ያልሆነ ወገንን መብትና ጥቅም የሚነካ መሆኑ ከተረጋገጠ ፍርዱ ይኸው ወገን ባለበት እንዲታይና በሕግና በማስረጃ የተደገፈ ሁኖ ሲገኝ እንዲነሳለት የሚደነግግ ነው፡፡ አቤቱታው የሚቀርብበት ሥርዓትም በቁጥር 359 ስር በተመለከተው መንገድ መሆን እንደአለበት የተቀመጠ ሲሆን ይህ ድንጋጌ የመቃወሚያ አቤቱታ አቀራረብ በክስ አመሰራረት አይነት ሁኖ ማስረጃ ዝርዝር ሁሉ ይህንኑ ስርዓት ማሟላት እንደአለበት ያስገነዝባል፡፡ የዚህ ድንጋጌ ይዘቱና መንፈሱ ሲታይ ክርክሩ መኖሩን ከጅምሩ እያወቀ ውጤቱን በመጠበቅ ከፍርዱ በኋላ የፍርድ መቃወሚያ የሚያቀርበውን ወገን አቤቱታውን በመቀበል ለማስተናገድ አስፈላጊ ያለመሆኑን ሁሉ ያስገነዝባል፡፡

ይህም የክርክር አቀራረብ በቅን ልቦና የተመሰረተ ሁኖ በአነስተኛ ወጪ፣ ጉልበትና አጭር ጊዜ ፍትሐዊነት ያለውን ውሳኔ ለመስጠት የሚቻልበት አግባብ እንዲኖር እና ሕግ አውጪ ከፈለገበት አላማ ጋር መጣጣም ያለበት መሆኑም የሚታመን ነው፡፡ እንግዲህ አቤቱታውን የሚያቀርበው ወገን የቅን ልቦና ተከራካሪ ሁኖ መሰረታዊ መብቱን ማስከበር የሚችልበት የስነ ስርዓት ሕግ አግባብ እንዲኖር ሕግ አውጪ የፈለገ ሲሆን ይህንኑ መመዘኛ የሚያሟላ አቤቱታ አቅራቢ የሚቃወመው ፍርድ ዋጋ ያለው፣ ያልተፈፀመ መሆን እንደአለበትም የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 358 ድንጋጌ ይዘት ያስረዳል፡፡ በሌላ አገላለፅ የፍርድ መቃወሚያ የሚቀርብበት ፍርድ ስልጣን ባለው ፍርድ ቤት ያልተሻረና አፈጻጸሙም ያልተጠናቀቀ ሊሆን እንደሚገባ ሕጉ ያሳያል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 93987 ቅጽ 17፣[2] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 358፣ 359

የሟች ሀብት ተጣርቶ በክፍፍሉ ላይ ውሳኔ ከተሰጠ በኋላ ውርሱ ሲጣራ ያልተሳተፈ የሟች ወራሽ ነኝ የሚል ወገን በፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 358 መሰረት መቃወሚያ ማቅረብ ያለበት በውርስ አጣሪው ሪፖርትና ሪፖርቱን ባፀደቀው ፍ/ቤት ሳይሆን የክፍፍሉን ጥያቄ አይቶ ውሳኔ ለሰጠው ፍርድ ቤት ነው፡፡

የውርስ አጣሪ ሪፖርት በፍርድ ቤት መጽደቅ በራሱ ፍርድ ሁኖ ለአፈፃፀም የሚቀርብ ሣይሆን እንደማስረጃ የሚያገለግል ነው፡፡ በመሆኑም ሪፖርቱ የማስረጃነት ዋጋ አለው ከተባለ ደግሞ የክፍፍል ክርክር ሲቀርብ በማስረጃነቱ ላይ ክርክር ቢቀርብ ክርክሩ መቅረብ ያለበት በውርስ አጣሪና ሪፖርቱን በአፀደቀው ፍርድ ቤት ነው ተብሎ ውድቅ የሚሆንበት ሕጋዊ ምክንያት የለም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 45905 ቅጽ 11፣[3] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 358፣ ፍ/ህ/ቁ. 944፣ 946፣ 956፣ 960

ተከራካሪ ወገኖች በፍርድ ቤት የሚያካሂዱትን ሙግት በማቋረጥ የሚያደርጉት የእርቅ ስምምነት በፍርድ ቤት ትእዛዝ ተረጋግጦና ለሚመለከተው ክፍል ይተላለፍ መባሉ የፍርድ ያህል አስገጃጅነት ያለው በመሆኑ እርቁን ያፀደቀው ፍርድ ቤት እርቁ ለሕግና ለሞራል ተቃራኒ አይደለም በእርቁ መሠረት ይፈፀም በማለት በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ መንገድ የሰጠውን ትእዛዝ በፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 358 መሰረት በእርቅ ስምምነቱ መብቴ ተነክቷል በሚል ወገን ተቃውሞ ሊቀርብበት የሚችል ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 83582 ቅጽ 15[4]

2. ንብረት እንዳይያዝ

በአፈጻጸም ንብረት እንዳይያዝ፣ እንዳይታገድ በንብረቶቹ ላይ መብት አለኝ የሚል በክርክሩ ተሳታፊ ያልሆነ ሶስተኛ ወገን የሚያቀርበው አቤቱታ

የፍ/ብ/ህ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ. 418 ድንጋጌ አስፈላጊነት የክርክሩ አካል ያልሆኑና ፍርድ ያላረፈባቸው የ3ኛ ወገን ንብረት ሳይረጋገጥ ለፍርዱ ማስፈፀሚያነት እንዳይውሉ ለመከላከልና ባንጻሩ ፍርዱን የመፈፀም ለማስተጓጉል (እንዳይፈፀም ለሚቀርቡት በቂ ላልሆኑ አቤቱታዎችም) እልባት የሚሰጥ ነው፡፡ በመሆኑም በተያዙት ንብረቶች ላይ መብት አለኝ የሚል ወገን የሚያቀርበውን መቃወሚያና አቤቱታ ተቀብሎ መመርመር እንዳለበት የተጠቀሰው ድንጋጌም በግልፅ ያሰፈረው ነው፡፡ ይህ ከሆነ የዚሁ አንቀጽ 418(3) የአራተኛው ቅጂ ባለይዞታነትን ለማስረዳት የፅሁፍ ማስረጃ መቅረብ እንዳለበት የሚደነግግ ቢሆንም የእንግሊዘኛው ቅጂ የስነ- ስርዓት ህጉ ደግሞ ይህንኑ አንቀጽ ሲገልጽ The Claimant or 0bjector Shall adduce evidence to Show that and the date of the attachment he had Some interest in or was possessed of the property attached ይላል፡፡ እንግዲህ ከዚህኛው የእንግሊዘኛ ቅጂ የምንረዳው ማስረጃ በማቅረብ ለአፈጻጸም የቀረበውን ንብረት ማስረዳት እንደሚቻል የሚገልጽ ነው፡፡ የአማርኛው ቅጂም ቢሆን ከፍ/ህ/ቁ/1193 (1) እና (2) ድንጋጌዎች ጋር ተደምሮ ሲታይ ሌላውን የማስረጃ አይነት በግልጽ እንዳይቀርብ የከለከለው ሆኖ አይታይም፡፡

ሰ/መ/ቁ 97094 ቅጽ 17፣[5] ፍ/ህ/ቁ. 1193(1) (2)፣ ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 418

በዋናው ክርክር የሚሰጠው ውሳኔ እና በውሳኔው መሠረት ለማስፈጸም የሚደረገው ሂደት የተለያዩ በመሆናቸው በሚቀርቡት መቃወሚያዎች ላይ የሚሰጡት ውሳኔዎችም የተለያዩ ናቸው፡፡ መቃወሚያ አቅራቢው መብቱ የተነካው በአፈጻጸም ሂደቱ ከሆነ ከአፈጻጸም ሂደቱ ጋር የተያያዘ መገፍትሄ ነው የሚሰጠው፡፡ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕግ ቁ. 418 መሠረት በሚቀርብ መቃወሚያ ላይ የሚሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕግ ቁ. 419 ተመልክቶአል፡፡ በዚህ መሠረት መቃወሚያው ተቀባይነት ያገኘ ከሆነ በአፈጻጸም የተያዘው ንብረት በከፊል ወይም በሙለ እንዲለቀቅ ትዕዛዝ ይሰጣል፡፡ ከዚህ አልፍ በአፈጻጸም የተያዘው ንብረት ለአንድ ወይም ለሌላው ተከራካሪ ወገን ይገባል የሚል ዳኝነት አይሰጥም፡፡ ከሁሉ በላይ ደግሞ በዋናው ክርክር የተሰጠውን ውሳኔ የሚሽር ወይም የሚያሻሽል ውሳኔ አይሰጥም፡፡ የዚህ አይነት ውሳኔ መስጠት የሚቻለው ዋናውን ውሳኔ በመቃወም አቤቱታ ሲቀርብ ነው፡፡ ይህ ደግሞ እራሱን የቻለ የአቀራረብ ሥርዓት እና የክርክር አመራር ሂደት ያለው ነው፡፡ በዚህ ረገድ ተገቢው ድንጋጌም በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕግ ቁ. 358 የተመለከተው ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 53607 ቅጽ 12[6]፣ ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 358፣ 418፣ 419

በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 418 አግባብ የተሟላ ክርክርና ማስረጃ ያቀረበ ወገን አቤቱታው በመደበኛ ሙግት እንዲከናወን እንዳይጠይቅ ሕጉ ግልጽ ክልከላ ያላደረገበት ሲሆን በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 421 ስር የተጠበቀው መብትም በሕጉ አግባብ የሚቀርቡ መቃወሚያዎች እንደተጠበቁ ሁነው አመልካቹ በምርጫው እንዲጠቀምበት የተቀመጠ እንጂ ይህንኑ ስርዓት እንዲከተል የግድ የሚደረግበት ያለመሆኑ ድንጋጌው በፈቃደኝነት የአቀራረፅ ስርዓት መቀመጡ አስረጂ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ 86133 ቅጽ 15[7]

የቀዳሚነት መብት አለኝ በሚል መቃወሚያ አቅርቦ ጥያቄው ውድቅ የተደረገበት ሰው በድጋሚ ክስ ማቅረብ የተፈቀደለት በአፈፃፀም ችሎት የንብረቱ ባለመብትነት በጭብጥነት ተይዞ በመደበኛው የሙግት ስርአት አይነት ከግራ ቀኙ ክርክርና ማስረጃ አንፃር ተመርምሮ ውሳኔ የሚሰጥበት ባለመሆኑ ይህንን እድል ለመስጠት ነው፡፡ አመልካቹ ይህንን መብት የሚያስከብርለት ሌላ ክስ የመሰረተ ከሆነ ግን የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 421 ክስ ለማቅረብ ስለሚፈቅድ ብቻ በተመሳሳይ ጉዳይ ዳግመኛ ክስ ማቅረብ የስነ-ስርአት ህጉ አላማ አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 37214 ቅጽ 9፣[8] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 421

 

 

 

[1] አመልካች ወ/ሮ አሰለፈች ይመር እና ተጠሪዎች እነ ወ/ሮ አስመረት ተወልደ /3 ሰዎች/ ሐምሌ 28 ቀን 2006 ዓ.ም.

[2] አመልካች እነ አቶ ዳንኤል ወንዳፈራ /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ አስናቀች ቦጋለ /4 ሰዎች/ ሐምሌ 18 ቀን 2006 ዓ.ም.

[3] አመልካች ሚስስ ሚላን ፑሲጂ /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ እነ ሐንድሬ ፒስ ማልጂ /2 ሰዎች/ ጥቅምት 3 ቀን 2003 ዓ.ም.

[4] አመልካች ወ/ሮ ወርቅነሽ ውብነህ ተጠሪዎች እነ ወ/ሮ አልማዝ ዓለሙ /3 ሰዎች አንደኛው በሌሉበት/ መጋቢት 27 ቀን 2005 ዓ.ም.

[5] አመልካች ወ/ሮ አስቴር አምባው እና ተጠሪዎች እነ አቶ አበባው ክፍሌ /2 ሰዎች/ ህዳር 8 ቀን 2ዐዐ7 ዓ.ም.

[6] አመልካች የምጥን መንደር መኖሪያ ቤቶች የህብረት ሥራ ማህበር እና ተጠሪዎች እነ ወ/ሮ ባየች አይገምት /3 ሰዎች 2 ሰዎች በሌሉበት/ ህዳር 14 ቀን 2003 ዓ.ም.

[7] አመልካች እነ አቶ ፍቅሩ ከበደ /11 ሰዎች/ እና ተጠሪ ወ/ሮ አስቴር አርአያ /2 ሰዎች/ ጥቅምት 20 ቀን 2006 ዓ.ም.

[8] አመልካች አቶ ተስፊዬ አለሙ እና ተጠሪ እነ ሐጂ ይማም ሙዘይን /3 ሰዎች/ የካቲት 25 ቀን 2002 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

ዳግም ዳኝነት—የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0

ዳግም ዳኝነት—የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

የመጨረሻ ውሳኔ ወይም ትዕዛዝ ከተሰጠ በኋላ ውሳኔው ወይም ትዕዛዙ ሐሰተኛ ማስረጃን መሰረት በማድረግ መሰጠቱ ሲረጋገጥ ጉዳዩ በድጋሚ /እንደገና/ የሚታይበት ስርዓት

በፍ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 6(2) ይግባኝ ሊቀርብበት የሚችል የመጨረሻ ውሳኔ ወይም ትዕዛዝ ከተሰጠ በኋላ ውሳኔው ወይም ትዕዛዙ የተሰጠው በሃሰት ተዘጋጅቶ የቀረበ ሰነድን፣ ሃሰተኛ የምስክርነት ቃልን፣ ወይም መደለያን ወይም ወንጀል ጠቅሶ የሆነ ተግባርን መሰረት አድርጎ መሆኑን አቤት ባዩ ሲረዳው ጉዳዩ በይግባኝ ከመታየቱ በፊት[1] ውሳኔውን የሰጠው ፍ/ቤት ራሱ ዳኝነቱን በድጋሚ እንዲያይ ጥያቄ ለማቅረብ መብት የሚሰጠው ነው፡፡ የድንጋጌው ሙሉ ይዘትና መንፈስ የሚያሳየው የመጨረሻው ፍርድ ከተሰጠ በሁዋላ ሀሰተኛ ሰነድ ወይም ሀሰተኛ የምስክርነት ቃል ወይም መደለያ እንደተደረገና አቤት ባዩም ፍርድ ከመሰጠቱ በፊት አስፈላጊውን ትጋት አድርጎ ለማወቅ ያለመቻሉን በሚገባ ለማስረዳት የሚችል የሆነ እንደሆነ፣ እነዚህ ጉዳዮች መኖራቸው ወይም መፈጸማቸው ታውቆና ተገልጾ ቢሆን ኖሮ ለፍርድ መለወጥ ወይም መሻሻል በቂ ምክንያት ሊሆኑ ይችል እንደነበር ለማስረዳት የቻለ እንደሆነ፣ የተሰጠ ፍርድ ሊያስለውጥ የሚችል አዲስ ማስረጃ ማግኘቱ ብቻ ፍርድ እንደገና እንዲታይ የማያደርግ መሆኑን፣ ማስረጃው ፍርዱን በማሳሳት ውጤቱን ያበላሸና ተገቢ ያልሆነ ድርጊትን የሚያሳይ መሆን ያለበት መሆኑን ነው፡፡

በመሆኑም ማስረጃው በሐሰት ተዘጋጅቶ የቀረበ ሰነድን፣ ሀሰተኛ የምስክርነት ቃልን ወይም መደለያን ወይም ወንጀል ጠቀስ ተግባርን መሰረት ያደረገ መሆንና ማስረጃው ፍርዱ በሚሰጥበት ጊዜ ፍርዱ እንደገና ይታይልኝ የሚለው ተከራካሪ ወገን ማስረጃው መኖሩን ያውቀው የነበረ ያለመሆኑ፣ ይግባኝ ቀርቦበት ከሆነ አዲስ ማስረጃው ለይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት ውሳኔ በሚሰጥበት ጊዜ ግምት ውስጥ እንዲያስገባ ይግባኙ ለቀረበለት ፍርድ ቤት መቅረብ ያለበት መሆኑ፣ የተገኘው አዲስ ማስረጃ የሀሰት ሰነድን፣ ሀሰተኛ ምስክርነትን፣ መደለያንና የመሳሰሉትን የሚመለከት ለመሆኑ ማረጋገጫ መኖሩን በሚጠቅስ ቃለመሐላ የተደገፈና ማስረጃው አስፈላጊው ትጋት የተደረገበት ቢሆንም ፍርዱ በተሰጠ ጊዜ በአመልካቹ ያልታወቀ መሆኑን የሚገልፅ መሆን ያለበት መሆኑ በቅድመ ሁኔታነት ሊሟሉ የሚገባቸው ጉዳዮች መሆናቸውን ድንጋጌው ያስገነዝባል፡፡

የዳግም ዳኝነት ጥያቄ ጥብቅ መለኪያዎች ያሉት መሆኑን ከድንጋጌው ይዘት መንፈስ መገንዘብ የምንችለው ጉዳይ ሲሆን የድንጋጌው ጥብቅ የመሆን አይነተኛ አላማም የተሰጡ ውሳኔዎችን አጣራጣሪነት ለማስወገድ መሆኑ ይታመናል፡፡ ስለሆነም የዳግም ዳኝነት ጥያቄ የቀረበለት ፍርድ ቤት ለውሳኔው መሰረት የሆነው ሰነድ ወይም ማስረጃ ሐሰተኛ መሆኑን ብቻ ሳይሆን በሕጉ የተመለከቱት ሁሉም መመዘዎችን አቤቱታ አቅራቢው ማሟላቱን በቅድሚ ሊያረጋገጥ ይገባል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 104028 ቅጽ 17፣[2] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 6

ፍርድ በድጋሚ እንዲታይ የሚጠይቅ ሰው ሀሰተኛ መረጃ የተሰጠው መንግስት በኃላፊነት ቦታ ላይ ባስቀመጠው ባለስልጣን እና በመንግስት አካል መሆኑን ከማስረዳት አልፎ የመንግስት ባለስልጣን ይህንን ህገወጥ ተግባር የፈፀመበትን ምክንያት እንዲያስረዳ ሊጠየቅ አይገባውም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 91968 ቅጽ 15፣[3] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 6፣ ወ/ህ/ቁ. 403፣ 405

የተፈጻሚነት ወሰን

አንድ ተከራካሪ ጠበቃ ወክሎ እንዲከራከር እንጂ የውርስ ሀብት ንብረት ስምምነት ለማድረግ የውክልና ስልጣን አልተሰጠውም በሚል ዳግም ዳኝነት እንዲታይ የሚቀርብ አቤቱታ በፍ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ. 6 ስር አይሸፈንም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 45839 ቅጽ 9[4]

የማስረዳት ግዴታ

በፍ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ. 6(1)(ሀ) መሰረት ጉዳዩ እንደገና እንዲታይ የቀረበው አቤቱታ ተቀባይነት የሚኖረው የመጨረሻው ፍርድ ወይም ውሳኔ ወይም ትዕዛዝ የተሰጠው በሐሰት ተዘጋጅቶ የቀረበውን ሰነድ ወይም ሀሰተኛ የምስክርነት ቃልን ወይም መደለያን ወይም ወንጀል ጠቀስ የሆነ ተግባርን መሰረት በማድረግ ሲሆን አቤት ባዩም ፍርድ ከመሰጠቱ በፊት አስፈላጊውን ትጋት አድርጎ ለማወቅ አለመቻሉን ማስረዳት የሚጠበቅበት ከመሆኑም በላይ በፊደል (ለ) እንደተጠቀሰውም እነዚህ የተዘረዘሩት ተግባሮች መፈጸማቸው ቢገለጽ ኖሮ ለተሰጠው ፍርድ መለወጥ ወይም መሻሻል በቂ ምክንያት ሊሆኑ ይችሉ እንደነበር አቤት ባዩ የማስረዳት ኃላፊነት አለበት፡፡

ሰ/መ/ቁ 89641 ቅጽ 15[5]

የሚቀርብበት ጊዜ

የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሔ/ቁ. 6 ተጨባጭ ውጤት ሊሰጥ በሚችል አኳኋን ሊተገበር የሚችለው ውሣኔው ሐሰተኛ እና ወንጀል ጠቀስ የሆኑ ተገባሮችን መሰረት በማድረግ የተሰጠ ነው የሚል አቤቱታ እስከቀረበበት እና በቂና አሣማኝ መሆኑን ፍ/ቤቱ እስካመነበት ድረስ ይግባኝ ይባልበትም አይባልበትም ያለልዩነት ሥራ ላይ እንዲውል በሚያስችል ሁኔታ ሲተረጎም ነው፡፡

ዳኝነት እንደገና እንዲታይ (Review of judgement) በሚል የሚቀርብ አቤቱታ አስቀድሞ በተሰጠ ውሣኔ ላይ ይግባኝ የተባለበት ነው በሚል ምክንያት ብቻ ውድቅ ሊደረግ እንደሚገባ ሰ/መ/ቁ. 16624 ተሰጥቶ የነበረው ትርጉም ተለውጧል፡፡ ስለሆነም ጥያቄው ጉዳዩ በይግባኝ ታይቶ ውሳኔ ከተገኘ በሁዋላም ቢሆን በቁጥር 6 ስር የተመለከቱት መመዘኛዎች ተሟልተው እስከተገኙ ድረስ መቅረብ ይችላል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 43821 ቅጽ 15[6]

የሚቀርብበት ፍርድ ቤት

ማንኛውም ውሳኔ የተሰጠበት ሰው በፍ.ስ.ስ.ሕ.ቁ. 6(1)(ሀ) እና (ለ) ስር የተመለከቱትን ሁኔታዎች ወይም ከእነዚህ አንዱን መሰረት በማድረግ የዳግም ዳኝነት አቤቱታውን ማቅረብ የሚችለው ፍርዱን ለፈረደው ወይም ትዕዛዙን ወይም ውሳኔውን ለሰጠው ፍ/ቤት ስለመሆኑ በፍ.ስ.ስ.ሕ.ቁ. 6(1) ስር በግልጽ ተመልክቶአል፡፡

የክልል ሰበር ሰሚ ችሎት ሐሰተኛ ማስረጃ ላይ ተመስርቶ ውሳኔ ሰጥቷል በሚል የዳግም ዳኝነት ጥያቄ ሊቀርብ የሚገባው ለሰበር ችሎቱ ሳይሆን መጀመሪያ ፍርዱን ለፈረደው የስር ፍ/ቤት ነው፡፡

የፍ.ስ.ስ.ሕ.ቁ. 6 ዓይነተኛ ዓላማ ተገቢ ሁኔታዎችና ፍሬ ነገሮች ተሟልተው መገኘታቸው ሲረጋገጥ በሀሰተኛ ማስረጃ፣ በመደለያና በመሰል ወንጀል ጠቀስ ድርጊቶች ምክንያት የተዛነፈውን ፍትሕ ወደነበረበት መመለስ ነው፡፡ ይህ ሂደት ከሰበር ችሎቶች የስልጣን ወሰን ውጪ የሆነው ፍሬ ነገርን የማጣራት እና ማስረጃን የመመዘን ተግባራት የሚከናወንበት በመሆኑ ምክንያት በሰበር ችሎት ሊስተናገድ የሚችልበት የህግ አግባብ ባለመኖሩ የተጠቀሰውን የስነ ስርዓት ድንጋጌ ዓላማ ለማሳካት ይቻል ዘንድ የሚኖረው አማራጭ የዳግም ዳኝነት አቤቱታው ፍሬ ነገር የማጣራት እና ማስረጃ የመመዘን ተግባራትን የማከናወን ስልጣን ባላቸው የስር ፍ/ቤቶች እንዲስተናገድ ማድረግ ይሆናል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 93137 ቅጽ 15[7]

ማስታወሻ

የችሎቱ አቋም በተመሳሳይ ጉዳይ በሰ/መ/ቁ. 08751 ቅጽ 6[8] ከሰጠው ውሳኔ ጋር አብሮ አይሄድም፡፡

በዚህ መዝገብ ችሎቱ የሰጠው ውሳኔ በተጭበረበረ ሰነድ ላይ በመመስረት እንደሆነ በመግለጽ አመልካች ያቀረቡትን አቤቱታ ተቀብሎ ግራ ቀኙን በማከራከር ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ ምንም እንኳን እንደገና እንዲታይ አቤቱታ የቀረበበት የችሎቱ ውሳኔ ተጭበረበረ በተባለው ሰነድ ይዘት ላይ ተመርኩዞ ባለመሰጠቱ የተነሳ አቤቱታው ውድቅ ቢደረግም በሰ/መ/ቁ. 93137 ከተያዘው አቋም አንጻር አቤቱታው ከጅምሩ ሊስተናገድ የሚገባው አልነበረም፡፡

ይግባኝ

ዳኝነት በድጋሚ እንዲታይ በሚቀርብ አቤቱታ ዳኝነቱ በድጋሚ ሊታይ አይገባውም ወይም ይገባዋል? በማለት ፍርድ ቤቱ በሚሰጠው ትዕዛዝ ወይም ብይን ላይ ይግባኝ ማቅረብ አይቻልም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 42871 ቅጽ 9፣[9] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 6(3) እና (4)

 

[1] በሰ/መ/ቁ 43821 (አመልካች የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን እና ተጠሪ አቶ አማረ ገላው ሐምሌ 30 ቀን 2002 ዓ.ም. ሰ/መ/ቁ. 43821 ቅጽ 9) ዳኝነት እንደገና እንዲታይ ጥያቄው መቅረብ ያለበት ከይግባኝ በፊት እንደሆነ በሰ/መ/ቁ 16624 ተሰጥቶ የነበረው የህግ ትርጉም ተለውጦ ከይግባኝ በኋላም ሊቀርብ እንደሚችል አቋም ተይዞበታል፡፡

[2] አመልካች ወ/ሮ ብዙአየሁ ያለው እና ተጠሪ አቶ ሲሳይ ካሴ የካቲት 17 ቀን 2008 ዓ.ም.

[3] አመልካች አቶ ግርማ ሰንበት አልቀረቡም እና ተጠሪ፡- ወ/ሮ አልማዝ ገብረየስ ታህሳስ 15 ቀን 200 ዓ.ም.

[4] አመልካች ወ/ሮ ይርጋአለም ከበደ ድና ተጠሪ እነ ወ/ሮ ፅጌ ሚካኤል / 5 ሰዎች/ ሚያዝያ 5 ቀን 2002 ዓ.ም

[5] አመልካቾች እነ ወ/ሮ ሐረገወይን ብርሃኑ /2 ሰዎች/ እና ተጠሪዎች እነ ወ/ሮ አዜብ ብርሃኑ /2 ሰዎች/ ጥቅምት 21 ቀን 2006 ዓ.ም.

[6] አመልካች ወ/ሮ ትርሐስ ፍስሐዬ እና ተጠሪ ወ/ሮ ዘነበች በሪሁን ጥር 5 ቀን 2002 ዓ.ም.

[7] አመልካች ወ/ሮ ብጥር ታገለ እና ተጠሪ ወ/ሮ አገር ተሰማ የካቲት 11 ቀን 2006 ዓ.ም.

[8] አመልካች ወ/ሮ አበበች በጅጋ እና ተጠሪ እነ ዶ/ር ተስፋዬ አካሉ /2 ሰዎች/ ግንቦት 26 ቀን 2000 ዓ.ም.

[9] አመልካች የቀድሞ ወረዳ 07 ቀበሌ 32 አስተዳደር ጽ/ቤት እና ተጠሪ ወ/ሮ ጆሮ ዋቅጅራ ጥር 12 ቀን 2002 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

ማመሳሰል/መለየት እና የህግ ትርጉም አስገዳጅነት

$
0
0

አዋጅ ቁ. 454/1997 በስር ፍ/ቤቶች ላይ ድርብ ግዴታዎችን ይጥላል፡፡ የመጀመሪያው አግባብነት ባላቸው ሁኔታዎች የሰበር ችሎትን የህግ ትርጉም መቀበልና ተግባራዊ ማድረግ ሲሆን የዚሁ ግዴታ ግልባጭ ገፅታ የሆነው ሁለተኛ ደግሞ አግባብነት በሌላቸው ሁኔታዎች ተፈጻሚ ከማድረግ መቆጠብ ናቸው፡፡ ለግዴታዎቹ ውጤታማነት ፈቃድ ብቻ ሳይሆን እውቀት ጭምር ይጠይቃል፡፡ ስለሆነም በየትኛውም እርከን የሚገኝ ፍርድ ቤት በበፊተኛው የማመሳሰል በኋለኛው የመለየት ክህሎት ሊኖረው ይገባል፡፡

የሰበር ችሎት ትርጉም በሁሉም እርከን ላይ በሚገኙ ፍ/ቤቶች አስገዳጅነት እንዲኖረው ህግ አውጪው በአዋጅ ቁ. 454/1997 ሲደነግግ የአስገዳጅነት የተፈጻሚነት ወሰኑ በምን ዓይነት ጉዳዮች ላይ ሊሆን እንደሚገባ ብዙም አላስጨነቀውም፡፡ እናም እንደዋዛ በዝምታ አልፎታል፡፡ ይህን ችግር ችሎቱ አስቀድሞ የተገነዘበው ይመስላል፡፡ ጠቅለል ባለ አነጋገር ቢሆንም በአስገዳጅነት እና በጉዳዮች ዓይነት መካከል ያለውን ዝምድና በሰ/መ/ቁ. 61221 ቅጽ 14[1] ለመለየት ተሞክሯል፡፡

በአዋጅ ቁጥር 454/1997 አንቀጽ 2(1) ስር እንደተመለከተው ከአምስት ያላነሱ የዚህ ችሎት ዳኞች ተሰይመው የሚሰጡት የሕግ ትርጉም ተመሳሳይ በሆኑ ጉዳዮች ላይ በማናቸውም እርከን የሚገኝን ፍርድ ቤትን የሚያስገድድ ነው፡፡ አንድ የሕግ ትርጉም ለተመሳሳይ ጉዳይ ገዥነት እንዲኖረው ለማድረግ ደግሞ በመሰረታዊ ነጥቦች ላይ ጉዳዮቹ መመሳሰል ያለባቸው ስለመሆኑ ከአስገዳጅ የሕግ ትርጉም ፅንሰ ሀሳብ የምንገነዘበው ነው፡፡

የትኞቹ ናቸው መሰረታዊ ነጥቦች የሚባሉት? የተሟላ ባይሆንም ለጥያቄው በሰ/መ/ቁ. 67924 ቅጽ 13[2] ምላሽ ቀርቧል፡፡ በዚሁ መሰረት፤

በሀገሪቱ ወጥ የሆነ የህግ አተረጓጎምና አፈጻጸም ማስፈን ይቻል ዘንድ እንደ አንድ ስልት ተቆጥሮ በወጣው በአዋጅ ቁጥር 454/97 ድንጋጌ መሰረት የፌደራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ከአምስት ያላነሱ ዳኞች ተሰይመው የሰጡት የህግ ትርጉም በበታች ፍ/ቤቶች የአስገዳጅነት ኃይል ወይም ባህርይ የሚኖረው ትርጉም በተሰጠበት እና ዳኝነት እንዲሰጥበት [በቀረቡት] ጉዳዮች መካከል የተነሳው የፍሬ ነገርና የህግ ጥያቄ የተመሳሰለ ሆኖ ከተገኘ ብቻ ነው፡፡

እርግጥ ነው፤ ህግና ፍሬ ነገር መመሳሰል አለባቸው፡፡ ፈታኙ ጥያቄ ምን ያህል መመሳሰል አለባቸው ነው፡፡ ሙሉ በሚሉ መመሳሰል አለባቸው ወይስ በአብዛኛው መመሳሰል አለባቸው? በአብዛኛው ከተባለስ መመሳሰሉ ሊኖር የሚገባው ለህግ ትርጉም ቀጥተኛ ተዛምዶ ያላቸው ጥቂት ግን ደግሞ መሰረታዊ ፍሬ ነገሮች መመሳሰል ነው ወይስ በቁጥር የሚበዙት ፍሬ ነገሮች መመሳሰል?

ለእነዚህ ጥያቄዎች እጥር ምጥን ያለ ምላሽ ማስቀመጥ ይከብዳል፡፡ ከማመሳሰል ጋር የተያያዙ ተያያዥ ጥያቄዎች የብዙ ዘመናት የዳበረ ልምድ ባላቸው የኮመን ሎው አገራት ሳይቀር በአንድ ቀመር አልተፈቱም፡፡ እያንዳንዱ ክርክር የግል ባህርያት አሉት፡፡ ተመሳሳይ ጉዳዮችን በተመሳሳይ መንገድ የመወሰን ስርዓት ከዓላማው አንጻር (ወጥነትና ተገማችነት) ብቻ እየተመነዘረ ከታየ የሚያስጎመጅ ገጽታ ቢላበስም አደጋዎችም እንዳሉት መዘንጋት የለበትም፡፡ ይሄን ጠቃሚ ነጥብ የሰበር ችሎት ሳይቀር አምኖ ተቀብሎታል፡፡

እንደሚታወቀው ክርክሮች የሚወሰኑት እንደ የግል ባህሪያቸው እየታየ ነው፡፡ በአንድ ጉዳይ የተነሣውን ክርክር እልባት ለመስጠት የተሰጠ ውሣኔ በሌላ ጉዳይ ለተነሣው ክርክርም እልባት ለመስጠት ያስችላል ብሎ ሙሉ በሙሉ መደምደም ትክክልም ተገቢም አይይደም፡፡[3]

በችሎቱ የ10 ዓመት ጉዞ በበርካታ ውሳኔዎች የተሰጡ የህግ ትርጉሞች በስር ፍ/ቤት በቀዳሚነት ብሎም በደጋፊነት እየተጠቀሱ አከራካሪ የህግ ጭብጦችን ለመፍታት የማይናቅ ፋይዳ ማበርከታቸው ባይካድም ተጨማሪ የክርክር ምንጭ እየሆኑ መምጣታቸውም በገሀድ የሚታይ ሐቅ ነው፡፡ በታተሙት 19 ቅጾች ውስጥ የስር ፍ/ቤት ለውሳኔው መሰረት ያደረገው የሰበር መዝገብ ከተያዘው ጉዳይ ጋር አግባብነት የለውም ተብሎ በችሎቱ የተተቸበት አጋጣሚ በየጊዜው መጨመር እንጂ መቀነስ አላሳየም፡፡ በተመሳሳይ መልኩ አግባብነት ያለው የህግ ትርጉም ሳይጠቀስ በዝምታ ታልፎ የሚሰጥ ውሳኔ ሰበር ደርሶ የሚታረምበት ክስተት ተደጋግሞ ታይቷል፡፡ በአጠቃላይ ሲታይ በአዋጅ ቁ. 454/1997 በቸልታ የታለፈው የጉዳዮች መመሳሰል አሁን አሁን ትኩረት የሚያሻው ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን የሰበር ችሎት ህግ በመተርጎም ብቻ ሳይሆን የራሱን ውሳኔዎች በመተርጎም ስራ መጠመዱ አይቀሬ ነው፡፡

የስር ፍ/ቤቶች በጥረትና በጥናት የታገዘ ልምድ እያካበቱ ሲመጡ የማመሳሰል ብቃታቸው በጊዜ ሂደት መዳበሩ አይቀርም፡፡ ሆኖም ማመሳሰል በቅንነትና በታማኝነት ካልታገዘ ውጤታማነቱ ይኮላሻል፡፡ ዳኞች ዳኝነት በሚሰጡበት መዝገብ ላይ ያሉትን ፍሬ ነገሮችና የህግ ነጥቦች ተመሳሳይ ይዘት ካለው የሰበር ውሳኔ ጋር በማነጻጸር የልዩነት ነጥቦችን ለማግዘፍ፤ የማይቀራረቡትን ደግሞ እንደምንም አጠጋግቶ ለማመሳሰል ሰፊ ስልጣን አላቸው፡፡ ከዚህ አድራጎት የሚገድባቸው ለዳኝነታዊ ስነ ምግባራቸው ያላቸው ተገዢነት ብቻ ነው፡፡ ዳኞች መሰረታዊ የህግ ስህተት የሚሰሩት ባለማወቅ ብቻ አይደለም፡፡ ከፊሎቹ በፍርድ ቤት የሚፈጸሙ ስህተቶች አንደኛውን ተከራካሪ ወገን ለመጥቀም ሆነ ተብሎ በማወቅ የሚሰሩ ስህተቶች ናቸው፡፡ እንዲህ ዓይነት ስህተቶች ሰበር ችሎት ብቻውን አያቃናቸውም፡፡ ልክ እንደ ህግ መተርጎም ሁሉ ማመሳሰልም ነጻ፣ ፍትሐዊና ገለልተኛ የዳኝነት ስርዓት ካልሰፈነ አያብብም፡፡ ይልቅስ በአጭር ይቀጫል፡፡

እዚህ ላይ የሰበር ችሎቱን ሚና ማውሳት ያስፈልጋል፡፡ ግልፅና ጥራት ያለው ውሳኔ ከሌለ ማመሳሰልን ይበልጥ አዳጋች ያደርገዋል፡፡ በስር ፍ/ቤቶች የተረጋገጡ ፍሬ ነገሮች አገላለጽ፣ መሰረታዊ የፍሬ ነገር እና የህግ ጥያቄዎችን በአግባቡ መለየት፣ ህጉ የተተረጎመበትን መንገድ ሳያወሳስቡ ማመልከት፣ መሰረታዊ የህግ ጥያቄው በየትኛው የህግ አተረጓጎም ስልት እንደተፈታ ማብራራት፣ የቋንቋውን የሰዋሰው ስርዓት የጠበቀ ቀላልና ሁሉም የሚረዳው አገላለጽ መጠቀም፣ አስገዳጅ የሆነውን ገዢ ደንብ (የህግ ትርጉም) አሳጥሮ ማጠቃለል በአጠቃላይ ለውሳኔው ይዘት ብቻ ሳይሆን ለውሳኔ አጻጻፍ መርሆዎችና ደንቦች ተገቢውን ቦታ መስጠት ወዘተ…ሁልጊዜ ከችሎቱ የሚጠበቁ ናቸው፡፡

ሰበር ችሎት የህግ ትርጉም ሰጠ ማለት የተተረጎመው ድንጋጌ አከራካሪነቱ ይቀራል ማለት አይደለም፡፡ ምክንያቱም በችሎቱ ትርጉም ላይ የአረዳድ ልዩነት ይፈጠራል፡፡ ለዚህም ነው ችሎቱ በሰ/መ/ቁ. 80350 ቅጽ 14[4] የጥንቃቄ መልዕክት ለማስተላለፍ የተገደደው፤

ይሁን እንጂ ይህ የሰበር ሰሚ አስገዳጅ የሕግ ትርጉም መንፈሱ በጥንቃቄ ታይቶ ግንዛቤ ካልተወሰደበት ከሕጉ ዓላማና መንፈስ ጋር የማይሄድ ውጤትን ማስከተሉ የማይቀር መሆኑ እሙን ነው፡፡

 

[1] አመልካች አቶ አከለ ምህረቱ እና ተጠሪ ማህበራዊ ዋስትና ኤጀንሲ መስከረም 22 ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም.

[2] አመልካች ወ/ሮ ምንያ ገ/ሥስሴ እና ተጠሪዎች ወ/ሪት መሠረት ዓለማሁ መጋቢት 26 ቀን 2004 ዓ.ም.

[3] ሰ/መ/ቁ. 41535 ቅጽ 12 አመልካች የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ተጠሪዎች እነ ግሎሪ ኃላፊነቱ/የተ/የግል ማህበር /4 ሰዎች/ ጥቅምት 3 ቀን 2003 ዓ.ም.

[4] አመልካች ሸራተን አዲስ እና ተጠሪ እነ አቶ ገናናው ከበደ /51 ሰዎች/ ጥቅምት 20 ቀን 2005 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

ተከሳሽን የሚጠቅም ቅጣት- የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0

በወንጀል የተከሰሰ ሰው አዲስ የወንጀል ህግ ከመውጣቱ በፊት በተፈፀመ ወንጀል ከተፈረደበት እና ሆኖም ግን ወንጀሉ በተፈፀመበት ጊዜ ስራ ላይ ከነበረው ወንጀል ህግ ይልቅ አዲሱ ህግ ለተከሳሹ ቅጣትን የሚያቀልለትና ተከሳሹን የሚጠቅም ሆኖ ከተገኘ ይሄው በአዲሱ ህግ ላይ ያለው ቅጣት የሚፈጸምበት ስለመሆኑ ከወንጀል ህጉ ቁ. 6 ድንጋጌ ይዘት የምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 95438 ቅጽ 6፣[1] ወ/ህ/ቁ. 6

የሰበር ሰሚ ችሎት ውሳኔ ተፈጻሚነት

በአንድ ወንጀል ተመሳሳይ የጥፋተኝነትና የቅጣት ውሳኔ ከተላለፈባቸው ተከሳሾች መካከል አንደኛው ባቀረበው የሰበር አቤቱታ መነሻነት ተጠቃሚ የሚያደርጋቸው ፍርድ ከተሰጠ ፍርዱ የሰበር አቤቱታ ላልጠየቁት ሆነ ጠይቀው አቤቱታቸው በአጣሪ ችሎት አያስቀርብም ተብሎ ውድቅ ለተደረገባቸው ሌሎች ተከሳሾችም ጭምር ተፈጻሚነት አለው፡፡

በተመሣሣይ የወንጀል ህግ ድንጋጌ ጥፋተኛ ተብለውና በወንጀሉ የነበራቸው ተሣትፍ እና ሌሎች ግላዊ ሁኔታዎች ተመሣሣይ ሆኖ በመገኘቱ ተመሣሣይ የሆነ የቅጣት ውሣኔ የተላለፈባቸው ሰዎች፣ የአንደኛው የሰበር አቤቱታ የሚጣራ የህግ ነጥብ ያለው መሆኑ ተገልጾ ለሰበር ችሎት ሰለቀረበና በውሣኔው ላይ መሠረታዊ የህግ ስህተት ያለበት መሆኑ ተገልጾ በሚሰጠው ፍርድ ተጠቃሚ የሚሆንበት የሌላኛው የሰበር አቤቱታ የሰበር አጣሪ ችሎት ለሰበር አያስቀርብም ተብሎ ውድቅ ስለተደረገበት ብቻ የፍርዱ ተጠቃሚ የማይሆንበትን አግባብ መከተል በህገ መንግስቱ አንቀፅ 25 እና በወንጀል ህጉ አንቀጽ 4 የተደነገገውን የእኩልነት መርህ የሚጥስና የሰበርን መሠረታዊ ዓላማ የማያሳካ ይሆናል፡፡

የወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት አንቀጽ 196 “የተፈረደባቸው ሰዎች ብዙ ሆነው አንድ ብቻ ይግባኝ ሲያቀርብ” የሚል ርዕስ ያለው ሲሆን የድንጋጌው ንዑስ አንቀጽ 1 ቃል በቃል ሲነበብ “ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት ያቀረበው ይግባኝ ስለተፈረደባቸው ብዙ ሰዎች የሚመለከት ሆኖ ይግባኝ ያለው ግን የተፈረደበት አንድ ሰው ብቻ በሆነ ጊዜ ከዚህ በታች የተመለከተው ሲሆን ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት የሚሰጠው ፍርድ ይግባኝ ያላሉትም ሰዎች ይግባኝ እንዳሉ ተቆጥሮ ይፈጸምላቸዋል ለማለት የሚቻለው፤ /ሀ/ በይግባኝ የተሰጠው ፍርድ ይግባኝ ባዩን የሚጠቅም በሆነ ጊዜና /ለ/ ተከሳሾች ይግባኝ ቢሉ ኖሮ በፍርድ እነርሱም ሊጠቀሙ ይችሉ ነበር የሚያሰኝ ሆኖ ሲገኝ ነው” የሚል ይሁንታ ያለው ነው፡፡

ይህንን ድንጋጌ አሁን ላለው የሰበር ስርዓት ለመጠቀም ካለው የሰበር ችሎት አደራጃጀትና አሰራር ጋር  በሚጣጣምና የሰበርን መሰረታዊ ዓላማ ሊያሳካ በሚችል መንገድ መተርጎምና ስራ ላይ ማዋል ይጠይቃል፡፡ ብዙ ተከሳሾች በአንድ ወንጀል የወንጀል ስራው ተካፋይና ግብረ አበር ሆነዋል ተብለው ክስ ቀርቦባቸውና፣ ጉዳዩን በመጀመሪያ ባየው ፍርድ ቤት እና በይግባኝ ባየው ፍርድ ቤት ወይም ይግባኝ ሰሚ ችሎት የተሰጠው የጥፋተኝነትና የቅጣት ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት አለበት በማለት አንደኛው ተከሳሽ የሰበር አቤቱታ አቅርቦ፣ አቤቱታው ለሰበር ችሎት ያስቀርባል ተብሎ በሰበር ችሎት ታይቶ፣ ጉዳዩን በመጀመሪያ ደረጃ ወይም በይግባኝ አይቶ ውሳኔ የሰጠው ፍ/ቤት የጥፋተኝነት ወይም የቅጣት ውሳኔ ወይም የጥፋተኝነትና የቅጣት ውሳኔው መሰረታዊ ህግ ስህተት አለበት ተብሎ ከተሻረ፣ ከተሻሻለ ወይም ከተለወጠና የሰበር ችሎት በመሻር፣  በማሻሻል ወይም በመለወጥ የሰጠው ውሳኔ የሰበር አቤቱታ ያላቀረቡትን ሌሎች በአንድ ጉዳይ የተከሰሱ ሰዎችን የሚጠቅም ሆኖ በተገኘ ጊዜ፣ ሰዎቹ ፍርዱን በመቃወም የሰበር አቤቱታ ባያቀርቡም ሰበር ችሎት በሰጠው ውሳኔ ወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ህግ ቁጥር 196 ንዐስ አንቀጽ 1 መሰረት ተጠቃሚ እንደሆኑ በሚያደርግ አግባብ ድንጋጌው መተርጎምና ስራ ላይ መዋል አለበት፡፡

በአንድ ወንጀል አድራጎት በወንጀል ህግ ስለወንጀል ተካፋይነት አድራጊነት ወይም ስለግብረአበርነት በተደነገጉት መሰረት በአንድ ላይ ፈጽመዋል ተብለው ክስ ከቀረበባቸው ጉዳዩን በመጀመሪያ ደረጃ ባየውና በይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት የጥፋተኝነትና የቅጣት ውሳኔ የተወሰነባቸው ሰዎች ብዙ ሰዎች ሁሉም በግላቸው የሰበር አቤቱታ አቅርበው የሰበር መዝገብ አስከፍተው ከፊሎቹ ያቀረቡት የሰበር አቤቱታና ያስከፈቱት የሰበር መዝገብ በሰበር ችሎት የሚቀርብ መሠረታዊ የህግ ስህተት ጭብጥ የለውም ተብሎ በአዋጅ ቁጥር 25/1988 አንቀፅ 22 መሠረት በሰበር አጣሪ ችሎት ውድቅ ቢደረግና ቢዘጋ የከፊሎቹ ወይም አንደኛው ተከሳሽ ያቀረበው የሰበር አቤቱታ በሰበር የሚጣራ መሠረታዊ የህግ ጭብጥ አለው ተብሎ ለሰበር ችሎት ቀርቦ የሰበር ችሎቱ የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኃላ የጥፋተኝነት ውሣኔውን ወይም የቅጣት ውሳኔውን ወይም የጥፋተኛነትና የቅጣት ውሣኔውን መሠረታዊ የህግ ስህተት አለበት በማለት የሰበር ችሎት ከሻረው፣ ካሻሻለው ወይም ከለወጠውና ውሳኔው የሰበር አቤቱታ አቅርበው የሰበር ማጣሪያ ችሎት የሚጣራ መሠረታዊ የህግ ስህተት ጭብጥ የለውም ብሎ አቤቱታውን ውድቅ ያደረገባቸውን ሰዎች የሚጠቅም ሆኖ በተገኘ ጊዜ የወንጀለኛ መቅጫ ሥነሥርዓት ህግ ቁጥር 196 ንዐስ አንቀፅ 1 ድንጋጌ ተፈፃሚ መሆን ይገባዋል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 101056 ቅጽ 18፣[2] ኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ህገ መንግስት አንቀጽ 25፣ ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 196

የዋስትና መብት አወሳሰን

በመርህ ደረጃ የተሻረ ሕግ ተፈፃሚነት የሌለው ሲሆን በተሻረ ሕግ ክስ ማቅረብ ደግሞ የመርሁ ልዩ ሁኔታ ነው፡፡ የተሻረውም ሕግ ተጠቅሶ በተከሳሹ ላይ ክስ የሚቀርበው ወንጀሉ ተሰርቷል በተባለ ጊዜ ሕጉ ሥራ ላይ ስለነበርና ተከሣሹም ያውቀዋል ተብሎ ስለሚገመትና በሚያውቀው ሕግ መሠረት መከራከር እንዳለበት የሕግ መርህ /Rule of legality/ ስለሚያስገድድ ነው፡፡ ከዚህም መገንዘብ የሚቻለው የተሻረው ሕግ የሚጠቀሰው ተከሳሹ ክርክሩን በአግባቡ ለመምራት እንዲያስችለው እንጂ ከዚህ ያለፈ ውጤት የሌለውና መጨረሻም ላይ ቅጣት የሚወሰነው ሥራ ላይ ባለ ሕግ ተመስርቶ መሆኑን ነው፡፡

የዋስትና ጉዳይ በዋናነት የሚታየው ቅጣትን መሠረት አድርጎ ነው፡፡ ተከሳሽ የተከሰሰው የዋስትና መብት በሚከለክል ድንጋጌ ቢሆንም ድንጋጌው የሚጠቀሰው ክርክሩን በአግባቡ ለመምራት ታስቦ እንደሆነ ሕጉ ይዞት የተነሳውን ዓላማ መገንዘብ ከተቻለ የዋስትናው ጉዳይ መታየት የሚገባው ሊወሰንበት ከሚችለው ቅጣት አኳያ መሆን እንዳለበት ይታመናል፡፡ ክርክሩ እልባት ካገኘ በኋላ ተከሳሹ የሚቀጣው በአዲሱ ሕግ መሠረት እንደሆነ ከወዲሁ በግልጽ መገንዘብ ከተቻለ ክርክሩ እስከሚጠናቀቅ ድረስ በእሥር ይቆይ ማለት ሕግ አውጭው የዋስትና መብት ሊከለክላቸው ያልፈለገውን ተከሣሾች የዋስትና መብት እንደመከልከል የሚቆጠርና ሕጉም የታለመለትን ዓላማና ግብ እንዳይመታ የሚያደርግ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 34077 ቅጽ 7[3]

[1] አመልካች አቶ ሰለሞን ደሣለኝ እና ተጠሪ የደቡብ ክልል ዐ/ህግ ግንቦት 07 ቀን 2006 ዓ.ም.

[2] አመልካች አቶ አይሸሽም ገብሬ እና ተጠሪ የፌደራል የሥነ ምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሐምሌ 30 ቀን 2007 ዓ.ም.

[3] አመልካች አቶ ሰይድ ይመር እና ተጠሪ የአማራ ክልል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን መጋቢት 9 ቀን 2000 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የአጣሪ ዳኝነት (judicial review) ስልጣን

$
0
0

የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሰበር ስልጣን በቀጥታ ከህገ መንግስቱ ይመነጫል፡፡ ሆኖም የስልጣኑን ወሰን የሚያሰምረው የህገ መንግስቱ አንቀጽ 80/3/ ሀ የአማርኛውና እንግሊዝኛው ቅጂ ግልጽ መፋለስ ይታይበታል፡፡ በአማርኛው ንባብ የሰበር ችሎት መሰረታዊ ‘የህግ ስህተት ያለበትን ማናቸውንም የመጨረሻ ውሳኔ’ የማረም ስልጣን ይኖረዋል፡፡ (ሰረዝ የተጨመረ) የእንግሊዝኛው ቅጂ ደግሞ over any final court decision የሚል አገላላጽ በመጠቀም ስልጣኑን ፍርድ ቤት የመጨረሻ ውሳኔ በሰጠባቸው ጉዳዮች ላይ ብቻ ይገድበዋል፡፡

የድንጋጌውን ይዘት ዝርዝር የሚወስነው ህግ ከእንግሊዝኛው ቅጂ ጋር ይስማማል፡፡ በፌደራል ፍርድ ቤቶች አዋጅ ቁ. 25/1988 አንቀጽ 10 የፌ/ጠ/ፍ/ቤት የሰበር ስልጣን የሚያገኝባቸው ሶስት ጉዳዮች ተዘርዝረዋል፡፡ እነዚህም፤

  • የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በይግባኝ አይቶ የመጨረሻ ውሳኔ የሰጠባቸው ጉዳዮች
  • የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት መደበኛ ችሎት የመጨረሻ ውሳኔ የሰጠባቸው ጉዳዮች
  • የክልል ጠቅላይ ፍ/ቤት መደበኛ ችሎት በይግባኝ አይቶ የመጨረሻ ውሳኔ የሰጠባቸው ጉዳዮች

በሶስቱም ጉዳዮች በውሳኔ ሰጭነት የተጠቀሱት ተቋማት መደበኛ ፍርድ ቤቶች ብቻ ናቸው፡፡ በኢ.ፌ.ዲ.ረ ህገ መንግስት አንቀጽ 80/3/ ሀ የእንግሊዝኛው ቅጂ ላይ court የሚለው ቃል እንዲሁ ይህንኑ ሀሳብ ያንጸባርቃል፡፡ ሆኖም የአማርኛው ንባብ ውሳኔ ሰጭውን በዝምታ አልፎታል፡፡ ላይ ላዩን ሲታይ ዝምታው ለህገ መንግስታዊ ትርጉም በር የከፈተ አይመስልም፡፡ ‘የመጨረሻ ውሳኔ’ የሚለው አገላለጽ ፍርድ ቤትን ታሳቢ አድርጓል ቢባል ብዙዎችን ያስማማል፡፡

ሆኖም ችግሩ ከቋንቋ አጠቃቀም ያልዘለለ የሚመስለው የአንቀጽ 80/3/ ሀ ድንጋጌ በተግባር ህገ መንግስታዊ ጥያቄ አስነስቶ የሰበር ችሎትን የአጣሪ ዳኝነት ስልጣን አስፍቶታል፡፡ በሰ/መ/ቁ. 43511[1] ከአዋጅ ውጪ የተወረሱ ንብረቶችን በተመለከተ ከፊል ዳኝነታዊ ስልጣን የተሰጠው የፕራይቬይታይዜሽን ኤጀንሲ ቦርድ ያስተላለፈው ውሳኔ በቀጥታ በሰበር እንዲታይ አቤቱታ ቢቀርብም አጣሪ ችሎቱ ጉዳዩ አስተዳደራዊ መሆኑን በመጠቆም ውድቅ አድርጎታል፡፡ ሆኖም በመዝገቡ ላይ አመልካች ሆነው የቀረቡት አቤቱታ አቅራቢዎች የውሳኔውን ህገ መንግስታዊነት በመሞገት ለህገ መንግስት ጉዳዮች አጣሪ አቤቱታ አስገቡ፡፡ አጣሪውም ለጥያቄያቸው አዎንታዊ ምላሽ ባለመስጠቱ የመጨረሻ አማራጫቸውን በመጠቀም ለፌዴሬሽን ምክር ቤት አመለከቱ፡፡ ም/ቤቱ የችሎቱን ስልጣን በማረጋገጥ መዝገቡን ወደ ሰበር ችሎት መለሰው፡፡ የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የቦርዱን ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት የማረም ስልጣን እንዳለው በማረጋገጥ የተሰጠው ይህ የም/ቤቱ ውሳኔ ‘የመጨረሻ ውሳኔ’ በሚል በህገ መንግስቱ አንቀጽ 80/3/ ሀ ላይ የተቀመጠውን አገላለጽ ከእንግሊዝኛ ቅጂ ፍጹም የተለየ ይዘትና መልዕክት ሰጥቶታል፡፡ በውጤቱም ከፍርድ ቤት ውጭ ያሉ ከፊል የዳኝነት አካላት ላይ የሰበር ችሎት የአጣሪ ዳኝነት ስልጣን እንዳለው አረጋግጧል፡፡

የም/ቤቱ ውሳኔ ህገ መንግስታዊ ፋይዳው ስር ነቀልና መሰረታዊ ነው፡፡ የስር ፍ/ቤቶችን የህግ ስህተት በማረም ብቻ ተወስኖ የነበረው የሰበር ችሎት በም/ቤቱ ‘በተጨመረለት’ ስልጣን ከፊል ዳኝነታዊ ስልጣን የተሰጣቸው የአስተዳደር አካለት የሚያስተላልፉትን ውሳኔ ጭምር የማረም የአጣሪ ዳኝነት ስልጣን ይኖረዋል፡፡ ችሎቱም ዳኝነታዊ የአስተዳደር ውሳኔዎችን ማረም ህገ መንግስታዊ ሚናው እንደሆነ በሌሎች ሁለት መዝገቦች በሰጣቸው ውሳኔዎች በተግባር አረጋግጧል፡፡

በሰ/መ/ቁ. 92546[2] የድሮው ፍትሕ ሚኒስቴር የአሁኑ ጠቅላይ ዓቃቤ ህግ የዲሲፕሊን ውሳኔ በቀጥታ ለሰበር ችሎት ቀርቦ ተሸሯል፡፡ አቤቱታ አቅራቢው በሚኒስትሩ የዲሲፕሊን እርምጃ የተወሰደበት ዓቃቤ ህግ ሲሆን ጉዳዩ በሰበር ችሎት ከመስተናገዱ በፊት በሌላ ፍርድ ቤት አልታየም፡፡ በመዝገቡ ላይ በችሎት የዳኝነት ስልጣን አከራካሪ ጭብጥ ሆኖ ባይወጣም የህገ መንግስቱ አንቀጽ 80/3/ ሀ እና አዋጅ ቁ፣ 25/88 አንቀጽ 10 ተጠቅሶ የቀረበውን አቤቱታ ችሎቱ መቀበሉ ሲታይ የአጣሪ ዳኝነት ስልጣኑ ጠንካራ መሰረት እየያዘ እንደመጣ እንደሆነ አስረጂ ነው፡፡ በሰ/መ/ቁ. 61221 ቅጽ 14[3] የተያዘው አቋም ይህንን ሀሳብ ያጠናክራል፡፡ በዚህ መዝገብ በሰፈረው ህግ ትርጉም በፍርድ ቤት እንዳይታዩ በመጨረሻ ማሰሪያ አንቀጽ (finality clause) ገደብ የተደረገባቸው ውሳኔዎች ሳይቀር በችሎቱ የአጣሪ ዳኝነት ስር እንዲወድቁ ተደርገዋል፡፡ ጉዳዩ የታየው አዋጅ ቁ. 714/2003 እና 715/2003 ከመውጣታቸው በፊት ሲሆን ቀድሞ በነበሩት የጡረታ ህጎች የማህበራዊ ዋስትና ጉባኤ ውሳኔ የመጨረሻ በመሆኑ በይግባኝ ሆነ በቀጥታ ክስ በመደበኛ ፍ/ቤቶች ሊታይ አይችልም፡፡

በሰ/መ/ቁ. 61221 የሰበር አቤቱታ የቀረበው የጉባዔውን የመጨረሻ ውሳኔ በመቃወም ነው፡፡ ሆኖም በችሎቱ የዳኝነት ስልጣን ላይ በተጠሪ በኩል ተቃውሞ በመቅረቡ የስልጣን ምንጭ አከራካሪ ጭብጥ ሆኖ ወጥቷል፡፡ ይህንን በማስመልከት ህገ መንግስቱን እና አዋጅ ቁ. 25/88 በማጣቀስ የሚከተለው የህግ ትርጉም ተሰጥቷል፡፡

ጉዳዩ በተነሳበት ጊዜ ስራ ላይ በነበረው ሕግ አግባብ ማህበራዊ ዋስትና ይግባኝ ሰሚ ጉባኤ የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻ ነው ከተባለ በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ መንግስት አንቀጽ 80(3(ሀ)) እና አዋጅ ቁጥር 25/1988 አንቀጽ 10 በተመለከተው አግባብ ለዚህ ሰበር ችሎት አቤቱታ ከማቅረብ የሚከለክል ሕጋዊ አግባብ የለም፡፡

 

[1] አመልካች የሟች አቶ ዋሲሁን መኮንን ሚስትና ወራሾች /8 ሰዎች/ እና ተጠሪ የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ ሰ/መ/ቁ. 43522 ቅጽ 14 ጥቅምት 23 ቀን 2005 ዓ.ም.

[2] አመልካች አቶ አብዱራዛቅ ኢብራሒም እና ተጠሪ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር ሰ/መ/ቁ. 92546 ቅጽ 15 ታህሳስ 18 ቀን 2006 ዓ.ም.

[3] አመልካች አቶ አከለ ምህረቱ እና ተጠሪ ማህበራዊ ዋስትና ኤጀንሲ መስከረም 22 ቀን 2005 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

ህጋዊነትና ካርታ ማምከን

$
0
0

ከጥቂት ዓመታት ወዲህ የባለቤትነት ማረጋገጫ የመስጠት ስልጣን ያላቸው አካላት ‘ካርታ ማምከን’ የሚሉት አዲስ ፈሊጥ አምጥተዋል፡፡ ፍርድ ቤቶችም ቃሉን በተውሶ እያዘወተሩት ወደ ህግ ቃል እየቀየሩት ነው፡፡ ይህ የማምከን እርምጃ እስከ 2005 ዓ.ም. ድረስ በተደጋገሚ ሲስተዋል የነበረ አሳዛኝ ክስተት ነው፡፡ ህገ መንግስታዊ ንብረት የማፍራት መብትን አደጋ ውስጥ የከተተው ‘ከመሬት ተነስቶ’ ካርታ የማምከን ተግባር በቅርብ ሆኖ የሚቆጣጠረው በመጥፋቱ የተነሳ አስተዳደሩ ከህገ ወጥነት ወደ ጋጠ ወጥነት ተሸጋግሯል፡፡ በአስረጂነት ከሚጠቀሱ የሰበር ችሎት መዝገቦች መካከል የሰ/መ/ቁ 17712 አንደኛው ነው፡፡ በዚህ መዝገብ አመልካች ሆኖ የቀረበው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጽ/ቤት ሲሆን ተጠሪ የወሮ ሳድያ እስማኤል ወራሾች ናቸው፡፡ የጉዳዩ አመጣጥና በሰበር የተሰጠው ውሳኔ በአጭሩ እንዲህ ይተረካል፡፡

ክርክሩ የተጀመረው በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ሲሆን ተጠሪዎች በውርስ የተላለፉላቸው በአዲስ አበባ የሚገኙ ሁለት የንግድ ቤቶችን ተከራይተው የሚሰሩባቸው ግለሰብ ቤቶቹን እንዲያስረክቧቸውና ያልተከፈለ ኪራይም እንዲከፍሉ በማለት ክስ ያቀርባሉ፡፡ ፍርድ ቤቱም መብታቸውን በማረጋገጥ ወሰነላቸው፡፡ ከውሳኔ በኋላ የአዲስ አበባ መስተዳደር ቤቶቹ በአዋጅ ቁጥር 47/67 የተወረሱና ከዚህ ቀደም ተሰጥቶ የነበረው የባለቤትነት ደብተር በአዲስ አበባ አስተዳደር ሥራና ከተማ ልማት ቢሮ የቤቶች ጉዳይ መምሪያ የተሰረዘ መሆኑን በመግለፅ በክርክሩ ውስጥ በተቃውሞ ገብቶ የባለቤትነት ጥያቄ ያነሳል፡፡

ጉዳዩን በመጀመሪያ ደረጃ እና በይግባኝ ያዩት የስር ፍ/ቤቶች ‘ቤቶቹ ስለመወረሳቸው የሚያረጋግጥ የመረካከቢያ ቅፅ አልቀረበም’ በሚል የአስተዳደሩን ጥያቄ ውድቅ አደረጉት፡፡ አስተዳደሩ የሥር ፍርድ ውሳኔዎች መሠረታዊ የሕግ ስህተት ስላለባቸው ይታረምልኝ በማለት የሰበር አቤቱታ በማቅረቡ የሰበር ችሎት የሚከተለውን ውሳኔ በድምፅ ብልጫ ሰጠ፡፡

በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1195 ንዑስ አንቀፅ 1 ላይ በግልፅ እንደተመለከተው የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለሃብትነትን በማወቅ በአስተዳደር ክፍል ለአንድ ሰው የተሰጠ የባለሃብትነት የምስክር ወረቀት ማስረጃ ለተሰጠው ሰው ለዚሁ የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለሃብት እንደሆነ እንደሚያስቆጥረው ተመልክቷል፡፡ በአንፃሩ ማስረጃው የተሰጠው ከደንብ ውጭ በሆነ አሰራር መሆኑ በተረጋገጠ ጊዜ ከፍ ብሎ በፍትሐብሔር ቁጥር 1195 ላይ የተመለከተው የሕሊና ግምት ፈራሸ እንደሚሆን የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1196 (1) ይደነግጋል፡፡ በያዝነው ጉዳይ በሕግ አግባብ ስልጣን ተሰጥቶት ይህን መሰሉን የባለሃብትነት ማስረጃ የሚሰጠው ክፍል ቁጥር 5127386 የሆነው የባለሃብትነት የምስክር ወረቀት የሰረዘው መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ በተሰረዘ የባለሃብትነት ምስክር ወረቀት ደግሞ የሚገኝ የባለሃብትነት መብት አይኖርም፡፡ የተጠሪ ወራሾችም አውራሻቸው ያልነበራቸውን መብት ሊወርሱ አይችሉም፡፡

ለንፅፅር እንዲረዳ በሓሳብ ልዩነት የተሰጠውን አስተያየትና ምክንያት ማየቱ ተገቢ ነው፡፡

አመልካች የአዲስ አበባ መስተዳደር በቤቶቹ ላይ መብት አለኝ የሚለው በመንግስት የተወረሱ ናቸው በሚል መሆኑን መዝገቡ ያስረዳል፡፡ ይሁን እንጂ ቤቶቹ በመንግስት የተወረሱ መሆናቸውን የሚያሳይለት ማስረጃ አላቀረበም፡፡ ለተጠሪዎች አውራሸ ተሰጥቶ የነበረው የባለቤትነት ደብተር ተሰርዟል ማለቱ ብቻውን ለእርሱ መብት የሚሰጠውና አቤቱታውም በፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 358 አግባብ እንዲሰተናገድለት ለማድረግ የሚያስችል አይደለም፡፡ በኔ እምነት የሥር ፍርድ ቤቶች ወደ ዋናው ጉዳይ ተመልሰው ክርክሩን እንደገና መመርመር ሳያስፈልጋቸው አመልካቹን ወደ ክርክሩ ለመግባት የሚያስችልህ መብት መኖሩን አላስረዳህም በሚል ከወዲሁ ጥያቄውን ውድቅ ማድረጋቸው የፈፀሙት የሕግ ስህተት የለም፡፡

የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1195 ግምት በፍ/ሕ/ቁ 1196 በተደነገገው መሠረት ማለትም በሕጉ መሠረት ፈራሸ ሊሆን ይችላል፡፡ የባለቤትነት ካርታው ከደንብ ውጭ የተሰጠ ከሆነ መሰረዙን ህግ ይፈቅዳል፡፡ ሆኖም የመሰረዝ ስልጣን ያለው አካል የካርታው አሰጣጥ ከደንብ ውጭ ስለመሆኑ የማስረዳት ግዴታውን ሊወጣ ይገባል፡፡ የአዲስ አበባ መስተዳደር ሥራና ከተማ ልማት ቢሮ የቤቶች ጉዳይ መምሪያ ካርታውን ሲሰርዝ ካርታው ከደንብ ውጭ የተሰጠ መሆኑን የማሳየትና የማስረዳት ግዴታ አለበት፡፡ ይህን ካላደረገ እርምጃው ከሥልጣን በላይ እንደመሆኑ በሕግ ፊት ዋጋ አይኖረውም፡፡ አመልካች ካርታው ከደንብ ውጭ ስለመሆኑ ወይም ቤቱ በአዋጅ ስለመወረሱ በክርክሩ ቢጠቅስም ከአባባል ያለፈ በተጨባጭ ማስረዳት አልቻለም፡፡ ስለሆነም የመሰረዝ ድርጊቱ የሕጋዊነት መርህን የሚጥስ፣ የሕግ የበላይነትን የሚጻረር፣ ከሥልጣን በላይ የሆነ ድርጊት ነው፡፡

የአብላጫው ድምፅ ይህን መሠረታዊ ጭብጥ አላነሳውም፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ካርታው በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1196 (1) መሠረት ተሰርዞ በምትኩ ለሌላ 3ኛ ወገን ሲተላለፍ ያ ሶስተኛ ወገን የቤቱ ሕጋዊ ባለቤት ስለመሆኑ መረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ የአዲስ አበባ መስተዳድር ባለቤትነቱ የተሰረዘውን የንግድ ቤት የራሱ ሃብት ሲያደርገው በሕጉ መሠረት የባለቤትነት መብት የተሰጠው መሆኑን ማረጋገጥ አለበት፡፡ በአዋጅ ቁ 47/67 ተወርሷል የሚል ከሆነ እንደተወረሰ በበቂ ማስረጃ ማሳየት አለበት፡፡ አመልካች የቤቱ ባለቤት ስለመሆኑ አሁንም በአብላጫው ድምፅ ላይ ጭብጥ ሆኖ ተነስቶ ድምዳሜ ላይ አልተደረሰበትም፡፡ በእርግጥ በተሰረዘ የባለሀብትነት የምስክር ወረቀት የሚገኝ የባለሀብትነት መብት አይኖርም፡፡ ከዚህ ድምዳሜ በፊት ግን የህግ የበላይነት ጥያቄ ምላሽ ማግኘት አለበት፡፡

ተጠሪዎች እየሞገቱ ያሉት የመሰረዙን ሕጋዊነት ነው፡፡ የተጠሪዎች ሙግት በአብላጫው ድምፅ ሰሚ አላገኘም፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ካርታው ከደንብ ውጭ ለአመልካች እንደተሰጠ ስላላስረዳ ድርጊቱ ሕገ ወጥ ወይም ከሥልጣን በላይ ነው፡፡ በቤቱ ላይ በሕጉ መሠረት ባለቤት እንደሆነ ስላላስረዳም ‘ከመሬት ተነስቶ በሌላ ሰው መብት ባለቤትነት ሊኖረው አይችልም፡፡ ይህን ሀሳብ በአነስተኛ ድምፅ አስተያየት ስንቋጨው፤

አመልካች እንኳንስ መብት ሊኖረው ቀድሞውኑ በተቃውሞ ወደ ክርክር ውስጥ እንዲገባ ሊፈቀድለት አይገባም ነበር፡፡

በሌላ ተመሳሳይ መዝገብ እንዲሁ ፍርድ ያረፈበት የባለቤትነት መብት አስተዳደሩ ስላመከነው መና ሆነ ቀርቷል፡፡ በሰ/መ/ቁ. 22719[1] ተጠሪ በሁለት የቤት ባለቤትነት ማረጋገጫ ደብተር /ካርታ/ የተመዘገቡ ሶስት የቤት ቁጥር የተሰጣቸው ቤቶች የራሳቸው መሆናቸው ተረጋግጦ በፍርድ ቤት ውሳኔ አርፎባቸው በአፈጻጸም መዝገብ ቤቶቹን ተረክበዋል፡፡ የፍርድ ሂደቱ እንደተጠናቀቀ አመልካች የቤት ማረጋገጫ ደብተሮቹን በመሰረዙ ተጠሪ ክስ አቀረቡ፡፡ በሰበር ችሎት በነበረው ክርክር ችሎቱ ተጠሪ መብታቸውን በፍርድ ቤት አስከብረውና አረጋግጠው የተፈጸመባቸው ዓይን ያወጣ ህገ ወጥ ተግባር ከማረምና የህግ የበላይነትን ከማስከበር ይልቅ ክስ የማቅረብ መብታቸውን ነፍጓቸዋል፡፡ ችሎቱ ለማመዛን እንደሞከረው፡

አመልካች የተጠሪን የባለቤትነት ማረጋገጫ ሰነዶች ከሰረዘ ተጠሪ አስቀድሞ በተጠቀሱት ቤቶች ላይ ባለመብት መሆኑን የሚያረጋግጡ ማስረጃዎችን በእጁ ማስገባት ይኖርበታል፡፡ ይህ መሠረታዊ ማረጋገጫ ሰነድ ወይም ማስረጃ ሳይኖረው ፍ/ቤት ሰነድ እንዲሰጠው እንዲወሰንለት መጠየቅ አይቻልም፡፡

በአጭር አነጋገር ቤቱን በአስተዳደሩ ህገ ወጥ ተግባር የተነጠቀ ሰው ቤቱ እንዲመለስለት የመጠየቅ መብት እንኳን የለውም፡፡

የሰበር ችሎት ዘግይቶም ቢሆን የሰ/መ/ቁ 17712 እና 22719 ውሳኔ ካገኙ ከሰባትና አምስት ዓመታት በኋላ ፍጹማዊ በሆነውና ፍጹማዊነቱንም ችሎቱ ይሁንታ በሰጠው የአስተዳደሩ ካርታ የማምከን ስልጣን ላይ ገደብ ለማበጀት ተገዷል፡፡ በሰ/መ/ቁ. 42501[2] ፍርድ ባረፈበት ጉዳይ ካርታ ማምከን ህገ ወጥነቱን ጠንከር ባሉ ቃላት እንደሚከተለው ገስጾታል፡፡

አንድ የአስተዳደር አካል በፍርድ ቤት ክርክር መረታቱን ከተረዳ በኃላ በሕጉ የተሰጠውን ስልጣን መነሻ በማድረግ ለፍርዱ መሰጠት መሠረት የሆነውን ማስረጃ ዋጋ በማሣጣቱ ምክንያት የፍርድ አፈፃፀም ዋጋ እንዲያጣ የማድረግ ውጤት በኢ.ፊ.ዲ.ሪ ሕገ መንግስት አንቀጽ 78/1/ እና 79/1/ እና /4/ ስር የተረጋገጠውንና የተከበረውን የነፃ ፍርድ ቤት መኖርንና የዳኝነት ስልጣን ትርጉም አልባ የሚያደርገው ነው፡፡

[1] አመልካች የአ/አ/ ከተማ አስተዳደር ስራ ከተማ ልማት ቢሮ ተተኪ የመሬት ልማትና አስተዳደር ባለስልጣን እና ተጠሪ አቶ ነጋሽ ዱባለ ጥር 14 ቀን 2000 ዓ.ም. ቅጽ 6

[2] አመልካች የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ እና ተጠሪ የአስር አለቃ ደምሴ ዳምጤ ወራሾች /3 ሰዎች/ የካቲት 28 ቀን 2005 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

በፍርድ የማይዳኙ ጉዳዮች

$
0
0

በፍርድ የማይዳኙ ጉዳዮችን (justiciability) በተመለከተ በፍርድ ቤቶች ዘንድ ያለው አረዳድ የፅንሰ ሀሳቡን ትክክለኛ ይዘት አያንጸባርቅም፡፡ በሰ/መ/ቁ. 51790 ቅጽ 12[1] በሰፈረው የሚከተለው ማብራሪያ መሰረት በፍርድ የማይዳኝ ጉዳይ ማለት ከፍርድ ቤት የዳኝነት ስልጣን ውጪ የሆነ ጉዳይ […]

The post በፍርድ የማይዳኙ ጉዳዮች appeared first on Ethiopian Legal Brief.


Selected Cassation decisions on Women

$
0
0

The Federal Supreme Court, in co-operation with Network of Ethiopian Women’s Association (NEWA) has published selected Cassation decisions related to women’s rights and women litigants. Click the link below to download the publication. […]

The post Selected Cassation decisions on Women appeared first on Ethiopian Legal Brief.

‘ሁከት ይወገድልኝ’ –የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0

የአንድ ንብረት ባለይዞታ የሆነ ሰው ይዞታውን ለመንጠቅ ወይም በይዞታው ላይ ሁከት ለመፍጠር የሚፈፀምን ማንኛውንም ድርጊት እንዲቆም ወይም ንብረቱ እንዲመለስለት የሚያቀርበው የይዞታ ክስ በፍ/ሕ/ቁ. 1149/1/ መሰረት የሁከት ይወገድልኝ ክስ መቅረብ የሚችለው አቤቱታ አቅራቢው […]

The post ‘ሁከት ይወገድልኝ’ – የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም appeared first on Ethiopian Legal Brief.

የሰበር ውሳኔዎች ግጭት

$
0
0
የሰበር ውሳኔዎች ግጭት የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከአምስት ያላነሱ ዳኞች በተሰየሙበት የሰበር ችሎት የሚሰጥ የህግ ትርጉም ለበታች የክልልና የፌደራል ፍርድ ቤቶች አስገዳጅነት እንዲኖረው አስገዳጅ ህግ ከወጣ (አዋጅ ቁጥር 454/1997) ከአስር ዓመት ዓመት በላይ አልፎታል፡፡ በእነዚህ ሁሉ ዓመታት ውስጥ ህጉና አፈጻጸሙ ለፍትህ ስርዓቱ ያበረከተው አዎንታዊ አስተዋጽኦ እና ያስከተለው ችግር በተመለከተ የዳሰሳና የክለሳ ጥናት ተደርጎ ውጤቱ ይፋ … Continue reading የሰበር ውሳኔዎች ግጭት

የመቃወም አቤቱታ—የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0
የመቃወም አቤቱታ —የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም 1. ፍርድ መቃወም ተካፋይ ባልሆነበት ክርክር የተሰጠው ውሳኔ መብቴን ይነካል በማለት አስቀድሞ ለአንድ ወገን የተሰጠውን ውሳኔ ለማሰረዝ በመቃወም አመልካች የሚቀርብ አቤቱታ የመቃወም አቤቱታ ሲቀርብ ክርክሩ የሚካሄደው በመቃወም አመልካች እና አስቀድሞ በተሰጠው ውሳኔ ተጠቃሚ በሆነው የመቃወም ተጠሪ በሚባለው ወገን መካከል ሲሆን የዚህ ዓይነቱ ክርክር የሚቀርብበት እና የሚመራበት ስርዓት እንዲሁም የዚህ … Continue reading የመቃወም አቤቱታ—የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

ዳግም ዳኝነት—የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0
ዳግም ዳኝነት—የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም የመጨረሻ ውሳኔ ወይም ትዕዛዝ ከተሰጠ በኋላ ውሳኔው ወይም ትዕዛዙ ሐሰተኛ ማስረጃን መሰረት በማድረግ መሰጠቱ ሲረጋገጥ ጉዳዩ በድጋሚ /እንደገና/ የሚታይበት ስርዓት በፍ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 6(2) ይግባኝ ሊቀርብበት የሚችል የመጨረሻ ውሳኔ ወይም ትዕዛዝ ከተሰጠ በኋላ ውሳኔው ወይም ትዕዛዙ የተሰጠው በሃሰት ተዘጋጅቶ የቀረበ ሰነድን፣ ሃሰተኛ የምስክርነት ቃልን፣ ወይም መደለያን ወይም ወንጀል ጠቅሶ የሆነ ተግባርን መሰረት አድርጎ … Continue reading ዳግም ዳኝነት—የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም
Viewing all 116 articles
Browse latest View live